• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ከኦነግ የተገነጠለው ኦዴግ ከኦዴፓ ጋር መቀላቀል ኢህአዴግን እና ግንቦት 7ን ወዴት ያመራቸዋል?

November 28, 2018 05:21 pm by Editor 2 Comments

“አዲሲቷን ኢትዮጵያ በጋራ ለመመስረት ተነስተናል። የቀድሞው የትግል ስልት አያዋጣም” በማለት “የኦሮሞ ዴሞክራሲያዊ ግንባር” (ኦዴግ) ODF የሚባል አዲስ ግንባር መጋቢት 22፤2005ዓም (ማርች 31/2013) ያቋቋሙት የቀድሞው የኦነግ ከፍተኛ አመራሮች የቀድሞውን ኦህዴድ የአሁኑን ኦዴፓን ተቀላቅለዋል። ከኦነግ ተገንጥሎ ኦዴግ የሆነው የሌንጮ ለታ ፓርቲ ኦዴፓን መቀላቀሉና በኢህአዴግና በግንቦት 7 ላይ የሚያስከትለው የፖለቲካ ተጽዕኖ ገና አልጠራም። ከዳውድ ኢብሣ ኦነግ ጋር እቀላቀላለሁ ያለው የመረራ ጉዲና ኦፌኮም መጨረሻው አልታወቀም።

የዛሬ አምስት ዓመት አካባቢ ከብሪታንያ፣ ከስዊትዘርላንድ፣ ከካናዳ፣ ከአውስትራሊያ፣ ከጀርመንና ከተለያዩ አገራት የተሰባሰቡ ቁጥራቸው 400 የሚጠጋ ተሰብሳቢዎች ባካሄዱት ውይይት ላይ ስለ ኦዴግ ማብራሪያ የሰጡት ሌንጮ አስፈላጊ የተባሉ ጥያቄዎች ተጠይቀው ነበር። ኢትዮጵያን “ኢምፔሪያሊዝም፣ ቅኝ ገዢና ጠላት” አድርገው በመሳል ጥያቄ የሰነዘሩትን ጨምሮ ስለ ቀጣዩ ትግል ትግበራና ስለ ኦሮሞ ህዝብ ነጻነት መከበር በስፋት ለተነሱ ጥያቄዎች አቶ ሌንጮ ለታ አስገራሚ መልስ ሰንዝረው ነበር።

“ያለፈውን በመውቀስ የትም አንደርስም። አሁን ማየትና ማሰብ ያለብን ወደፊት ነው። ሌሎች ወገኖችን አግልለን ብንታገል የትም አንደርስም። ያለፈው የትግል መንገድ ስህተት ነበር” ብለዋል። ስለ ኦሮሞ ህዝብ ነጻነት መከበር ሲናገሩ “የሁሉም ኢትዮጵያዊ መብት ካልተከበረ የኦሮሞ መብት ብቻውን ሊከበር አይችልም” በማለት መመለሳቸውን ለማወቅ ተችሏል።

የኦሮሞ ነጻ አውጪ ግንባር ከፍተኛ አመራርና ጸሐፊ የነበሩት አቶ ሌንጮ ለታ አዲስ ያቋቋሙትን ድርጅት ይዘው አዲስ አበባ እንደሚገቡ የዚያን ጊዜ አስረግጠው ተናግረው የነበሩት አቶ ሌንጮ ድርጅታቸው ኢትዮጵያ ገብቶ ለመታገል መወሰኑ ለምን ወሬ እንደሚባል እንዳልገባቸውም የዚያን ጊዜ አመላክተው ነበር።

ቀጥሎም በ2006ዓም ጥር 5 ቀን ከጀርመን ድምጽ የአማርኛ ፕሮግራም ጋር ቃለ ምልልስ ያደረጉት አቶ ሌንጮ “ኖርዌይ ተቀምጠን ምን እናደርጋለን? ሃገር ቤት ገብተን እንታገላለን” ሲሉ ወደ አገር ቤት ለመመለስ መወሰናቸውን ግልጽ አድርገዋል። “ይሳካል?” በማለት ጠያቂው ላቀረበው “ይሳካል አይሳካም ተብሎ ወደ ትግል አይገባም” በማለት አቶ ሌንጮ ማምረራቸውን በሚያሳብቅ ሁኔታ መልስ መስጠታቸው ይታወሳል።

በቀጣይም ወደ አገርቤት ከገቡ በኋላ ህወሓት/ኢህአዴግ በጠበቁትና በፈለጉት ልክ አላንቀሳቅስ ስላላቸው ጥለው ወጥተው ነበር። የዛሬ ሰባት ወር አካባቢ እንቁላሉን ከውስጥ በሰበሩት የለውጥ ኃይሎች በውጭ አገራት ለሚገኙት ተቃዋሚ ኃይሎች በሙሉ ባቀረቡት ጥሪ መሠረት ኦዴግ አዲስ አበባ ገብቷል።

ወደ ኢትዮጵያ ከመምጣቱ በፊት አገባቡ አብሮት ጥምረት ከፈጠረው አርበኞች ግንቦት 7 በፊት በመሆኑ ለወደፊቱ ከግንቦት 7 ጋር የሚኖረው ግንኙነት እንዴት እንደሚሆን የድርጅቱ የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባልና የድርጅቱ ቃል አቀባይ አቶ ሌንጮ ባቲ ቢቢሲ አማርኛ ለጠየቃቸው ምላሽ ሰጥተው ነበር። “ለሃገር ግንባታ እና ዴሞክራሲ ዕድገት ከሚሠራ ማንኛውም ፓርቲም ሆነ ግለሰብ ጋር አብሮ ለመስራት ዝግጁ ነን። ከማንኛውም ቡድን ጋር መሥራታችን ይቀጥላል። አቋማችንን የሚቀይር ነገር የለም” ብለዋል።

ዛሬ ህዳር 19፣ 2011 የኦሮሞ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኦዴፓ) እና የኦሮሞ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኦዴግ) ተዋህደው መቀጠል የሚያስችላቸውን የመግባቢያ ስምምነት ሰነድ ተፈራርመዋል። ፋና እንደዘገበው ስምምነቱን የኦዴፓ ምክትል ሊቀመንበር አቶ ለማ መገርሳና የኦዴግ ሊቀ መንበር አቶ ሌንጮ ለታ ተፈራርመዋል።

የኦሮሞ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ ምክትል ሊቀመንበር አቶ ለማ መገርሳ ሁለቱ ፓርቲዎች በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ የራሳቸው ታሪክና አስተዋጽኦ እንዳላቸው ጠቅሰዋል። ተበታትኖ መጓዙ ለህዝቡም ሆነ ለፖለቲካ ፓርቲዎቹ አድካሚ በመሆኑም እንደየፓርቲዎቹ የአስተሳሰብ ቀረቤታ በመጣመርና በመዋሃድ ለሃገር ግንባታ መረባረብ እንደሚያስፈልግም ነው የተናገሩት። የፓርቲዎቹን ውህደት ህዝቡ ሲጠይቅ እንደነበር ያነሱት አቶ ለማ፥ ፓርቲዎቹም ተወያይተው ውሳኔ ላይ መድረሳቸውን አውስተዋል።

የኦሮሞ ዴሞክራሲያዊ ግንባር ሊቀመንበር አቶ ሌንጮ ለታ በበኩላቸው፥ የኢትዮጵያን ፌዴራሊያዊ ስርዓት ዴሞክራሲያዊ በማድረግ የተረጋጋና ሰላማዊ የአፍሪካ ቀንድን መገንባት እንደሚቻል ገልጸዋል። አቶ ሌንጮ አያይዘውም የኦሮሞ አንድ መሆን ለሃገር ግንባታም ቢሆን ትልቅ አስተዋጽኦ ይኖረዋልም ነው ያሉት።

የኦዴፓ የገጠር ፖለቲካ አደረጃጀት ሃላፊ አቶ አዲሱ አረጋ ስምምነቱን አስመልከቶ በሰጡት መግለጫ፥ ሁለቱ ፓርቲዎች የኦሮሞ ህዝብ አንድ እንዲሆኑ ባቀረበላቸው ጥሪ መሰረት በዛሬው እለት በጋራ መስራት የሚያስችላቸውን የውህደት የመግባቢያ ስምምነት እንደተፈራረሙ አንስተዋል። አያይዘውም ኦዴፓ ከኦዴግ ጋር የህገ ደንብ፣ የስትራቴጅ እና የፕሮግራም ልዩነት የሌለው በመሆኑ በጋራ እንደሚሰራም ጠቁመዋል። በቀጣይም ከሁለቱ ፓርቲዎች የቴክኒክ ኮሚቴ ተቋቁሞ በዝርዝር ጉዳዮች ላይ ውይይት ይደረጋል ብለዋል። በጋራ ለመስራት የሚደረገው የውህደት ሂደት እንደሚቀጥል ያነሱት አቶ አዲሱ፥ አሁን ላይም ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር የተጀመሩ ውይይቶች መኖራቸውን ጠቅሰዋል።

በሁሉም ዓይነት መስክ እታገላለሁ ሲል የነበረው ግንቦት ሰባት ሰሞኑን ከአርበኞች ግንባር ጋር ተፋትቷል። ከሌንጮ ለታ ኦዴግ ጋር የመሠረተው ፈዛዛ ጥምረትም እስካሁን ይህ ነው የሚባል ውጤት ሳያሳይ አሁን ደግሞ ኦዴግ ከኦዴፓ ጋር በመቀላቀል ብቸኛ አድርጎታል። ግንቦት 7 ከኢህአዴግ ጋር መቀላቀል የሚችልበት የርዕዮት መስመር የለውም። ከዚህ ሌላ ግንቦት 7 ፓርቲ ሳይሆን ወደ ፓርቲ ምሥረታ የሚሄድ ንቅናቄ ነው። ኦዴግ በዚህ ከኦዴፓ ጋር ባደረገው ስምምነት ግንቦት ሰባትን ጥሎ የሄደ ይመስላል፤ ምክንያቱም ግንቦት 7 ከኦዴግ ጋር ጥምረት ሲፈጥር ለኦዴግ ኅብረብሔራዊ ቁመና ለመስጠት በምላሹ ደግሞ ለራሱ የኦሮሞን ድጋፍ ለማግኘት የታሰበ እንደሆነ ብዙዎች የሚስማሙበት ነው። በመሆኑም ግንቦት 7 የአቋምና የአስተላለፍ አካሄዱን በማሳመር በአገር ውስጥ እየተንቀሳቀሱ ከሚገኙ ፓርቲዎች ጋር መቀላቀል የግድ ይሆንበታል። ይህ ደግሞ አስቀድሞ ከቅንጅት ጋር ውኅደት ሲፈጠር ፓርቲዎቹን ለከፍተኛ ችግር የዳረገው ዓይነት የስልጣን ሽኩቻ ውስጥ እንዳያስገባው ካሁኑ ፍርሃቻ አለ።

ከላይ “በጋራ ለመስራት የሚደረገው የውህደት ሂደት” ይቀጥላል በማለት የተናገሩት አቶ አዲሱ፥ “አሁን ላይም ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር የተጀመሩ ውይይቶች መኖራቸውን” መጥቀሳቸው ኦዴፓ በኦሮሞ ስም የተደራጁ ሌሎች ፓርቲዎችን እየጠቀለለ ግዙፍ የኦሮሞ ፓርቲ ይሆናል የሚል ግምት እንዲሰጠው አድርጓል። ከዚህ አኳያ በርዕዮት፣ በፖለቲካ ፕሮግራም፣ ወዘተ ከሌንጮ ኦዴግ ጋር ተመሳሳይነት ያለው የመረራ ጉዲና ኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ ከዳውድ ኢብሣ ኦነግ ጋር ውኅደት ለመፍጠር በመሥራት ላይ እንደሆኑ በመስከረም ወር ላይ አስታውቀው ነበር። እስካሁን ግልጽ ባይሆንም ይህ አካሄድ ኦዴፓን ያገዝፈዋል፤ ወይም ኦፌኮንና ኦነግን በጥምረት የኦዴፓ ግምባር ቀደም ተፎካካሪ ያደርጋቸዋል።

በሌላ በኩል ይህ የኦዴግና የኦዴፓ ውህደት በግንቦት 7 ላይ የሚስከትለው የፖለቲካ ጫና ብቻ ሳይሆን በኢህአዴግ ላይ የሚያመጣው ተጽዕኖ ምን እንደሚሆን ገና አልጠራም። ኦዴግ ኢህአዴግን በመቃወም ከአብዮታዊ ዴሞክራሲ ርዕዮት የተለየ አካሄድ ሲከተል የቆየ ፓርቲ ነው። ኦዴፓ ደግሞ በቅርቡ ካካሄደው የስምና መሰል ለውጦች አኳያ ኢህአዴግን በስም ብቻ የተሸከመ እንጂ በገሃድ የኢህአዴግ ካባውን አሽንቀጥሮ የጣለ ፓርቲ ሆኗል። ይህ ውህደት ደግሞ ኦዴፓ በጣም ራሱን ከኢህአዴግ አግልሎ እየሄደ ለመሆኑን እንደማሳያ ሆኖ ቀርቧል። ከዚህ አንጻር የኢህአዴግ መጻዒ ዕድል “በክብር” ወደ ሙዚየም መግባት ወይም የህወሓት ወንበዴዎች “ታላቁ መሪ” እንደሚሉት መለስ ወደ ከርሰ መቃብር መውረድ ይሆናል። ሁሉም ጉዳይ በቅርቡ መስመር የሚይዝ ይሆናል።


ማሳሰቢያ፤ በተለይ በስም ወይም በድርጅት ስም እስካልተጠቀሰ ድረስ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ™ ላይ የሚወጡት ጽሁፎች በሙሉ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ™ ንብረት ናቸው። ይህንን ጽሁፍ ለመጠቀም የሚፈልጉ ሁሉ የዚህን ጽሁፍ አስፈንጣሪ (link) ወይም የድረገጻችንን አድራሻ (http://staging.goolgule.com/) አብረው መለጠፍ ከጋዜጠኛነት የሚጠበቅና ህጋዊ አሠራር መሆኑን ልናሳስብ እንወዳለን።

Print Friendly, PDF & Email

60

SHARES
Share on Facebook
Tweet
Follow us
Share
Share
Share
Share
Share

Filed Under: News Tagged With: Full Width Top, ginbot 7, Middle Column, odf, odp, ofc, olf, opdo

Reader Interactions

Comments

  1. Sergute Selassie says

    November 29, 2018 01:24 pm at 1:24 pm

    https://sergute.blogspot.com/2018/11/blog-post_55.html
    https://sergute.blogspot.com/2018/11/blog-post_42.html
    ጤና ይስጥልኝ እንዴት ናችሁ። በሳል ትንተና ነው። ወድጀዋለሁኝ። የአቶ ሌንጮ ለታ ልክን አቅምን የማወቅ ተመክሮ ከስህተት ለመማር መቁረጥ ከእነሱ በስንት ዘመን ካነሰው ኦህዴድ ይምራኝ አቅምህ ከእኔ የላቀ ነው ብሎ መቀበል አዲስ የታሪክ ምዕራፍ አዲስ የታሪክ የፊደል ገበታ ነው። መጀመሪያውን ነገር የለውጡ መሪዎችን ለማደናቀፍ ካድሬ ወጀብ ሚዲያ አላሰለፉም። ሁሉንም አብረው ለመስራት አቅም ከነበረው ጋር ለመስራት አቅም የሚባለውን ነገር ለክተውል። ይህንንም ውጭ እያሉ አገራዊ ንቅናቄው ደካማ መሆኑን ገልጸዋል ዘሃበሻ ላይ ወጥቶ ነበረት፤ የፖለቲካ ድርጅት ፓርቲ ፍልስፍና ዕውቀታቸውን ለማየትም ችያለሁ ፓርቲ የገብያ ማህበር አለመሆኑን ያምኑበታል፤ በማመከር ደረጃ ከዶር አረጋይ በርሄ ይልቅ አቶ ሌንጮ ለታ ብቁ ናቸው። ሃሳብ አላቸው። ግንቦት ፯ ዕድል የለሽ ድርጅት ነው፤ የተመሰረተበት ቀን የኮከብ ቆጠራ ያስፈልገዋል ወይ የመሪ ለውጥ ያስፈልገዋል፣ ቅብዕ የማይዘለል ስለሆነ። ብርቴ ቅብዕ ስላላት የተዳፈነው ቅብዕዋ ጧፍ ሆኖ የፈሯትን እንሆ ልትመራ እዮር ሰጣት። ብረት መዝጊያ የሆነ ዘመድ፤ ሚዲያ ሉላዊ የሆነ የነፃነት ታጋይነት የብዕር ተሸላሚነት ደጀን የላትም። ልቧ ጥቁር አይደለም እንድልቧ ድንግልና ቅንነቷ አወጣት። ሌላው ግንቦት ፯ ፖሊሲ የለውም ስለዚህ ስብስብ ውስጥ ለመግባትም ፈተና አለበት። ዒላማው በአውሮፓ እና በምዕራባውያን ተጽዕኖ አውራ ፓርቲ ሆኖ አገር መሪ መሆን ነበር ይህን ዕድሉን የአማራ ተጋድሎና የኦሮሞ ፕሮቴስት ቀማው፤ ገብቶት በነበረውም ያልተገባ እልህ ብዙ ሃብቱን የመንፈስ አጥቷል። ታሪክ አይሸለምም ለዚህ ተጋድሎ የአማራና የኦሮሞ ልጆች ተገብረዋል። ዘር አልባ እስከ መሆን ይህን ያዳመጡ የተቀበሉ ለማ አብይ ገዱ አንባቸው ደግሞ መንፈሳችን ሸለምናቸው። በራሱ ጊዜ ተው እያልን የጻፍ ሰዎች አድማጭ አልነበረም ከግንቦቶች፤ ይህም ሳይብቃ የዛሬ ዓመት የሚዲያ የብራና ተጋድሎ ይዅው ሊንኩ ልይላ አስጣ ገባ ገቡ፤ ደግነቱ ራሱ የአብይ ካቢኔ እያወቀ ሙሉ አክብሮት ለግንቦት ፯ ሰጥቶታል። የአመራር ጥበብ እንዲህ ይገለጣል፤ የዶር መራራ የአቶ ዳውድ ኢብሳ መንገድ ዕውቅና እራሱ ለለውጡ አልሰጡም። መታበይ አያለሁ። ችግራቸው ይሄ ነው። በለማ ሥር መሆን ከብዷቸዋል የሚሹትም ኦዴፓ አሁን ያገኘው ብሄራዊ አገርን የመምራት ዕድል ለእኛ ይገባናል ባዮች ናቸው። የተዳፈነው እረመጥ ይህ ነው። ውስጣቸው እየነደደ ነው። ግንቦት ፯ ኢህአዲግን ወደ ህብረ ብሄር ፓርቲ መግፋት ነው ቀጣዩ ዕድሉ። ይህ ከሆነለት አንድ ቀን አያድርም ሲቀላቀል። ምክንያቱም ተጽዕኖ ፈጣሪ ግለሰቦች የነፍሱ ማደሪያ ናት። አብሶ ዶር ለማ መገርሳ እና ዶር አብይ አህመድ ያገኙት ተቀባይነት ባይፈቅደውም መንገዱ ከተገኘ ጉዝጓዝነቱ ሎተሪ ነው ልግንቦት ፯። የሚገፋው አቅም አይደለም ዕለቱን በሉላዊ ብቃት የታምራት ጌታ ስላደረጉት፤ እነ ዶር ገዱ እና ዶር አንባቸው ግን ለማጓጓዣ ካልሆነ ሙሉ ዕድላቸውን አከርካሪ የሰበሩ ስለሆነ የቅብ ሂደት ይከተላሉ ብየ አስባለሁ። አብን ሌላው በሙሉ ብቃት ዓላማውን የተረዳ ሌላም ጉልባታም ድርጅት አለ፤ ስለዚህ የኦዴፓ ጥንካሬ ከብአዴን ውጭ አውራ ሆኖ አራጊ ፈጣሪ ሆኖ የመቀጠል አቅም አይኖረውም ሁሎችንም የኦሮሞ ድርጅቶች ኦዴፓ ጋር ቢዋህድ። ራሱ ለውጡ ነፍስ አግኝቶ ተፎካካሪዎች የተስተናገዱበት አማራ መሬት ላይ ነው። በብዙ ሁኔታ አማራ መሬት ላይ የኢትዬጵያዊነት ጽኑ መንፈስ ሌላ ቦታ የለም። ከዚህ በላይ መሳሪያ ደግሞ የለም። Kenbete (ቀንበጥ) ብሎግ ይጎብኙ፤ የዛሬ ዓመቱ ጉግስ ይህ ነበር።
    https://sergute.blogspot.com/2018/05/17_2.html
    https://sergute.blogspot.com/2018/05/blog-post_2.html
    https://sergute.blogspot.com/2018/05/18_2.html
    https://sergute.blogspot.com/2018/05/24.html
    https://sergute.blogspot.com/2018/05/blog-post_26.html
    https://sergute.blogspot.com/2018/05/24.html
    https://sergute.blogspot.com/2018/05/20.html
    https://sergute.blogspot.com/2018/05/01.html
    https://sergute.blogspot.com/2018/05/05.html
    https://sergute.blogspot.com/2018/05/10_2.html ወዘተ …

    Reply
  2. Hibret Selamu says

    November 30, 2018 06:41 pm at 6:41 pm

    ኢትዮጵያ አንድ ሐገር ሆና እንድትቀጥል ከተፈለገ፤ በዘር አከፋፈል ሥርኣት ሕዝቡ ተፋጥጦ እየተገዳደለ እንዲቀጥል ማድረግ አይቻልም፡፡ በአንድ በኩል የጎሰኝነት አከላለል እያጠናከሩ በሌላ በኩል ኢትዮጵያዊነትን ማጠናከር አይቻልም፡፡ ስለዚህ አቶ ለማና ክቡር ዶር አቢይ ኢትዮጵያን በአጉል ዘረኛነት ሳይሆን ሕዝቡን በሚያስተባብርና በሚያቀራርብ ሥርአት በማቀናጅት አንድነቱና መተባበሩ እንዲጠናከር ቢያመቻቹ ይሻላል፡፡

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • ጃዋርና በቀለ መታሠራቸው ተሰማ June 30, 2020 09:17 am
  • አገራዊ መድረክ ውጪ ድብቅ ውይይትን አንቀበልም June 17, 2020 06:57 am
  • ዴክሳሜታሶን! የኮሮና መድሀኒት June 17, 2020 06:49 am
  • የሰኔ 14ቱ ቀለበታዊ የፀሃይ ግርዶሽ በኢትዮጵያ! June 17, 2020 06:38 am
  • የግብፅ የአባይን ውሃ ብቻዬን ልጠቀም ግትር አቋም ድርድር እንቅፋት ሆኗል June 10, 2020 07:15 am
  • የቴድሮስ “ሥልጣን” – የመጨረሻው መጀመሪያ!? April 12, 2020 02:48 am
  • በብዛት የትግራይ ተወላጆች የሚጠቀሙበት የኤርትራ ስደተኛ ካምፕ ሊዘጋ ነው March 18, 2020 08:37 pm
  • እየተፈረካከሰ ያለው አንጋፋው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ March 18, 2020 08:09 pm
  • ኮሮና አዲስ ጉድ መዘዘ – ከቻይና በፊት በአሜሪካ ቁጥራቸው የማይታወቅ ሰዎችን ቀጥፏል March 16, 2020 11:41 pm
  • የኮንዶሚኒየም ቤቶች በደላሎችና በመመሪያ ሰጪዎች ኔትዎርክ እየተቸበቸበ ነው! ታከለ የት ናቸው? March 9, 2020 10:18 am
  • ኤርሚያስ ለገሠ ከባለአደራ ተባረረ March 9, 2020 08:09 am
  • ድፍድፍ ሲቀል ይንሳፈፋል፤ ምሁር ሲዘቅት ይመራል፥ March 7, 2020 11:24 pm
  • ኢትዮጵያዊ ምን ይመስላል? በምንስ ይመሰላል? March 7, 2020 10:29 pm
  • WHY I WROTE “MONEY, BLOOD AND CONSCIENCE” March 4, 2020 11:15 pm
  • አድዋ፤ የጥቁር ሕዝብ ድል! March 2, 2020 11:24 am
  • ፊታውራሪ ገበየሁ ገቦ (አባ ጎራው) March 2, 2020 11:12 am
  • የኦነግ ሁለት መልክና ሦስት ግብሮች – ቃርሚያው ኃይል ቅጥር ነፍሰገዳይ ሆኗል February 25, 2020 11:26 pm
  • በቡራዩ “የጃል ማሮ” ፎቶ ጨረታ አፈናከተ፤ “ቡራዩ ሆኖ ከሃዲን ማሞካሸት አይቻልም” ነዋሪዎች February 17, 2020 09:13 pm
  • “ዲቃላ” የፍረጃ ፖለቲካ በኦሮሚያ የኃይል አሰላለፉን እየቀየረ ነው February 13, 2020 11:58 pm
  • “ከዚህ በኋላ ማናቸውንም በወንጀል ድርጊት ውስጥ የሚሳተፉ አካላትን” አንታገስም – ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ February 13, 2020 05:07 pm
  • “እኛ ማንም ተሳዳቢ እንዲመጣብን አንፈልግም” የጅማ ነዋሪ February 13, 2020 09:28 am
  • “ወላጆቻችሁ ሰላማዊ ሰልፍ በሕዝቡ ያስደርጉልን” – አጋቾች February 11, 2020 07:53 pm
  • “ወንጀል የፈጸመም ያስፈጸመም ተይዞ ለህግ ይቀርባል፤ ምርመራም ተጀምሯል” February 11, 2020 06:59 pm
  • ጃዋር ወደ መጨረሻው “የትግል” ስልቱ – አማራን ማበጣበጥ! February 10, 2020 11:54 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2026 · Goolgule