• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

“በሃይማኖት ማስገደድ የለም!”

April 20, 2015 05:44 am by Editor Leave a Comment

የፌስቡክ ወዳጃችን Abubeker Siraj ከዚህ በታች ያለውን ጽሁፍ ከመልዕክት ጋር ልከውልናል፤ ሁሉንም እንዳለ አቅርበነዋል፡፡ ለፌስቡክ ወዳጃችን Abubeker Siraj ምስጋናችንን እናቀርባለን፡፡

ሰላም እና በረከት ቅኑን መንገድ በተከተለ ላይ ሁሉ ይሁን

ጎልግሎች ሆይ! እኔ አንድ አንባቢያቹ ነኝ ከአዲስ አበባ። ፅሁፎቻቹን አነባለው አደንቃለው። ከምንም በላይ አገር ወዳድነታችሁ እና ሚዛናዊነታችሁን ሳላደንቅ አላልፍም። ዛሬ አንዲት ጉዳይ ላወራቹ ፈልጌ ነበር። እሱም አሁን ከዚህ በታች ያለው ሊንክ ላይ የሚገኘው የወንድሜ ኢብኑ ሙነወር (Ibnu Munewor) ፅሁፍ የሚያጠነጥነው ሰሞኑን አይ ኤስ አይ ኤስ በፈፀመው ዘግናኝ ኢ ሰብአዊ ተግባር ላይ ሲሆን በጥቅሉ እኛ ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ከዚህ አፀያፊ እና ዘግናኝ ተግባር ፍፁም የፀዳን መሆናችንን እና ከክርስቲያን ወገኖቻችን ጋር በመቻቻል እየኖርን መሆኑን የሚያትት ነው።

ስለዚህ ከቻልቺፍ ልክ ከዚህ ቀደም ተመሳሳይ ወንድም ስለ ሴኪዩላሪዝም ፅሁፍ ፅፎ እንዳወጣቹትና ሚዛናዊነታቹን ለሙስሊሙ ህብረተሰብ እንዳሳያቹት ይህንንም ፅሁፍ አንብቡትና ፅሁፉን ሼር ብታደርጉት።

የአብሮነታችንን ቁርኝት ይበልጥ ያጠናክራል ብዬ እገምታለሁ።

አመሰግናለሁ፡፡

ሰሞንኛው የ ISIS ዘግናኝ ድርጊትን በተመለከተ ጥቂት ያቅሜን ልበል!

በረጂሙ የኢስላም ታሪክ የሌሎች እምነት ተከታዮችን አስገድዶ ወደ ኢስላም ማስገባት አልተመዘገበም፡፡ ይሄ ሙስሊም ያልሆኑ ነገርግን ሚዛናዊ የሆኑ ምሁራን ሳይቀር በጥናቶቻቸው ያሰፈሩት ሐቅ ነው፡፡ ሙስሊሞች እስፔንን ለ736 አመት ተቆጣጥረዋት ቆይተዋል፡፡ ነገር ግን አስገድዶ ማስለም ቢኖር ኖሮ አንድም ክርስቲያን እንዳይቀር ማድረግ በቻሉ ነበር፡፡ ህንድን ከአንድ ሺህ አመት በላይ ሲገዟት ቆይተዋል፡፡ ነገር ግን አስገድደው ሰዎችን ወደ ኢስላም እንዲገቡ አላደረጉምና አሁንም ድረስ ሙስሊሞች ቁጥራቸው ከጠቅላላው ህዝብ አንፃር ሲታይ እጅግ አነስተኛ ናቸው፡፡ በአለም ላይ ትልቁ የሙስሊም ህዝብ ያለባት ሀገር ኢንዶኔዢያ ነች፡፡ ነገር ግን አንድም የሙስሊም ወታደር እግር አልረገጣትም፡፡ ማሌዢያ ብዙሃኑ ህዝቧ ሙስሊም ነው፡፡ ነገር ግን አንድም የሙስሊም ወታደር እግር አልረገጣትም፡፡ በአረቡ አለም በርካታ ሚሊዮን ክርስቲያኖች ዛሬም ድረስ አሉ፡፡ ሙስሊሞች በታሪካቸው አስገድደው ያሰልሙ እንዳልነበር ህያው ምስክሮች ናቸው፡፡ የፀረ ሴማዊነት እንቅስቃሴ ከፍቶ የሁዶች ከአውሮፓ ምድር ሲፈናቀሉ በብዛት ወደ ሙስሊሙ አለም ሲጎርፉ ነበር፡፡ እምነታቸውን በግድ ሊቀይሯቸው ቀርቶ ተቀብለው ነበር ያስተናገዷቸው፡፡ ሙስሊሞች ይህን ሁሉ ሲያደርጉ የነበረው “በሃይማኖት ማስገደድ የለም!” የሚለውን ቁርኣናዊ መልእክት እየተገበሩ ነበር፡፡ ነገር ግን ለገዛ እምነታቸው ባይተዋር በሆኑ ደም በጠማቸው ሰው-በላ ጭራቆች እየተፈፀመ ያለው ሰቅጣጭ ድርጊት ሳቢያ እምነታችን ጥላሸት እየተቀባ ነው፡፡

እናዝናለን!!

በግፍ ለተገደሉት ወገኖች እናዝናለን፡፡ እሱን አይተው ለተሳቀቁትና ቅስማቸው ለተሰበሩ ሁሉ እናዝናለን፡፡ እነዚህ ነቀርሳዎች ፈፅሞ ከአለም አቅም በላይ አይደሉም፡፡ ሆኖም ግን ከስር ነቅሎ ለመጣል በመስራት ፋንታ ያለ ሃላፊነት ወሬ ማራገብን በመረጠው አለም እናዝናለን፡፡ ከከንፈር መምጠጥ ያለፈ ነገር ማድረግ ባለመቻላችንም እናዝናለን፡፡

የነዚህ ነቀርሳዎች ዳፋ የሚተርፈው ከማንም በላይ ለሙስሊሞች ነው፡፡ አንድ ቂላቂል ፂማም ባፈነዳ ቁጥር በአለም ላይ ያሉ ፂማሞች ሁሉ የሰቀቀን ህይወት ያሳልፋሉ፡፡ በበቀል እርምጃ ህይወታቸውን ያጣሉ፡፡ የፈረንሳዩን አደጋ ተከትሎ አሜሪካ ላይ የተፈፀመውን እናስታውሳለን፡፡ አንዲት ቂላቂል ከሰላማዊ መሃል እራሷን አጥፍታ በምትፈፅመው አረመኔያዊ ተግባር በመላው አለም ያሉ እህቶቻችን ለፈተና ይጋለጣሉ፡፡ መውጫ መግቢያ ያጣሉ፡፡ የሚገርመው ደግሞ ብዙዎቹ ይህን ኢ-ሰብኣዊ ድርጊት የሚፈፅሙት አካላት ከሃይማኖቱ ጋር ይሄ ነው የሚባል ትውውቅ የሌላቸው መሆኑ ነው፡፡ አዎ እነዚህ ሰላማዊ ዜጎችን በአሰቃቂ ሁኔታ እያጠቁ ያሉቱ አካላት በኢስላም ስም ከማስተጋባታቸው ባለፈ አብዛሃኞቹ ኢስላማዊ ነፀብራቅ እንኳን አይታይባቸውም፡፡ ፂማቸውን የላጩ፣ ልብሳቸውን የሚጎትቱ፣ አልፎም በሚገርም ሁኔታ ጆሯቸው ላይ ሎቲ ያንጠለጠሉ ሁሉ አይተናል፡፡ ገፈቱ የሚተርፈው ግን እነዚህ ኢስላማዊ ነፀብራቆች ለሚታዩበት ሙስሊም ነው፡፡ በጣም እናዝናለን!! ይሄ ሸውራራ እይታ ይበልጥ ችግሩን ሲያውሰበስብ በገሃድ እየተመለከትን ነው፡፡ መቼስ ሰላም ዜና አይሆንምና የቢሊዮኖች ሰላማዊነት አልፎም ድርጊቱን ማውገዝ ሳይሆን የነዚህ ነቀርሳዎች ድምፅ ነው ከእምነታችን ጋር ተያይዞ ጎልቶ የሚሰማው፡፡

ከምንም በላይ ከሙስሊሙ የሚጠበቅ ሃላፊነት አለ!!

የአስተሳሰብ ወረራን መመከት ከባድ ነገር ነው፡፡ ይሄ ጭራቃዊ አስተሳሰብ ከናካቴው ቦታ እንዳይኖረው የምንችለውን ሁሉ የማድረግ ሃላፊነት አለብን፡፡ ይሄ መርዛማ አስተሳሰብ ከእምነታችን ጋር እንደማይሄድ በቅድሚያ በውል ልናውቅ ይገባል፡፡ ከማንም በበለጠም ልናወግዘው ይገባል፡፡ ይሄ ደም-መጣጭ አስተሳሰብ ከሌሎች በበለጠ ኢላማ የሚያደርገው ሙስሊሞችን ነው፡፡ ይህን ደግሞ በተለያዩ ሀገራት በተግባር ሲፈፀም አይተነዋል፡፡ መስጂድ ውስጥ ሶላት ላይ ያሉ ሰጋጆችን እንኳን በጅምላ ከመጨፍጨፍ እንደማይመለሱ በተጨባጭ አረጋግጠናል፡፡ እነዚህ ነቀርሳዎች ለሐጅ በሚጓዙ ሰዎች ላይ ሳይቀር ሲዝቱ ታዝበናል፡፡ እነዚህ ሰው-በላዎች ጥፋታቸውን የሚያጋልጡ ታላላቅ ዑለማዎችን ጭንቅላታቸውን እንቆርጣለን እያሉ በትዊተር ሲዝቱ ተመልክተናል፡፡ ስለዚህ አደጋው ከማንም በላይ የራሳችን አደጋ ነው፡፡

ትላንት ጋዜጦቻችን እንደ ቢላደን ያሉ የጥፋት አውራዎችን ጀግና እያደረጉ ሲያቀርቡልን ነበር፡፡ ከእምነቱ ቀኖና ይልቅ ለስሜታቸው ያደሩ መሀይማን እይታን በማስቀደም የበርካቶችን አስተሳሰብ ሲበርዙ ቆይተዋል፡፡ የትላንቱ ሸውራራ ስብከት ሰለባ የሆኑ አካላት ከእምነቱ ታላላቅ አስተማሪዎች ይልቅ የአጥፊዎቹ ድምፅ ከፍ ብሎ ይሰማቸዋልና አስተሳሰባቸውን የመግራት ሃላፊነት አለብን፡፡ ህዝባችን የግል ኪሳቸውን ከማድለብ ባለፈ ብዙም የማያሳስባቸው የነገር አውታሮች ሰለባ እንዳይሆን ብዙ ልንሰራ የግድ ይለናል፡፡

የዚህ ቆሻሻ አስተሳሰብ ተከታዮች በእምነታችን ውስጥ ፍፁም ቦታ የላቸውም፡፡ የዚህን የጥፋት አንጃ ተከታዮችን ነብዩ ሙሐመድ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም “የጀሀነም ውሾች” ሲሉ ነው የገለፁዋቸው፡፡ ህይወት እንኳን ቢያስከፍል እስከ ደም ጠብታ ልንታገላቸው እንደሚገባም አበክረው አሳስበዋል፡፡ ሙታኖቻቸውንም “ከሰማይ በታች እጅግ ክፉ ግዳዮች” ሲሉ ነው የገለፁዋቸው፡፡ እነሱን እየታገለ ለሞተም እድለኛ እንደሆነም ጠቁመዋል፡፡ የፈለገ አምልኮትን ቢያበዙ፣ የፈለገ ፈሪሀ አላህ ቢመስሉም እምነት ከጉረሯቸው ያልወረደ ጥራዝ ነጠቆች እንደሆኑም ነው አስረግጠው የነገሩን፡፡

በዘመናችን ተመሳሳይ አስተሳሰብ የያዙ አንጃዎችንም ታላላቅ ዑለማዎች አጥብቀው ነው የኮነኗቸው፡፡ ታላቁ ሙፍቲ ዐብዱልዐዚዝ ኢብኒ ባዝ (አላህ ይማራቸውና)፡ ኡሳማ ቢን ላደንን የጥፋት መንገዶችን ሆን ብሎ የሚከተል በምድር ላይ ጥፋትን ለማንገስ ከሚጥሩ ሰዎች አንዱ እንደሆነ ነው የገለፁት፡፡ ግና ይህን ሐቅ ምን ያክሉ ህዝባችን ነው የሚያውቀው፡፡ የዋህነት ይበቃናል! አሜሪካንን ያወገዘ ሁሉ ልክ አይደለም፡፡ ቂልነት ይበቃናል!! የእምነታችንን ቀኖና እየጣሱ ለእምነት መቆርቆር የሚባል ሳይንስ የለም፡፡ እንጂማ እስኪ የትኛው የቁርኣን አንቀፅ ነው ሰላማዊ ህዝብ መሃል ቦምብ ታጥቆ በመግባት ህፃን ከአዋቂ፣ ሴት ከወንድ፣ ሳይለዩ በጅምላ መጨረስን ጂሃድ የሚያደርገው? እስኪ የትኛው ነብያዊ አስተምህሮ ነው ሰላማዊ ተማሪዎችን ምንም በሌሉበት በጅምላ መጨፍጨፍን ቅዱስ እልቂት የሚያደርገው? እስኪ የትኛው ኢስላማዊ ማስረጃ ነው የሆነ ሀገር ሙስሊሞችን ስላጠቃ ብቻ ምንም ንክኪ የሌለውን የዚያችን ሃገር ዜጋ ገድለህ ጎትተው፣ አስከሬኑን አቃጥለው የሚለው? ነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ለዘመቻ የሚያሰማሯቸው ሶሐቦቻቸውን እንኳን “ሴቶችን፣ ህፃናትን፣ ሽማግሌዎችን፣ በአምልኮት ቦታዎች የተገለሉ አካላትን እንዳይነኩ አላዘዙምን? ሌላው ቀርቶ ዛፎችን እንኳን እንዳይቆርጡ አላሳሰቡምን? ታዲያ ኢስላማዊውን ህግ እየጣሱ ለኢስላም መቆርቆር አለን? እነዚህ የደም ጥማት ያሰከራቸው ጀዝባዎች ግን የእምነቱን ህግ እየጣሱ ስለ እምነቱ ይደሰኩራሉ፡፡ “በእሳት የሚቀጣው የእሳት ጌታ (አላህ) ብቻ ነው” የሚለው የሙሐመድ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም አስተምህሮ ሳያቆማቸው ከነህይወት በእሳት ያቃጥላሉ፡፡ ግና አያፍሩም በእምነት ስም ጥፋታቸውን ይነዛሉ፡፡

ይህን ፅሁፍ ለሚያነቡ በተለያየ መልኩ ሀላፊነት ላይ ላሉ ሁሉ!

  1. የነዚህ ሰው-በላዎች ድርጊት አብዛሃኛውን ሙስሊም እንደማያስደስት አታጡትምና ስለዚህ ልደሰኩር አልፈልግም፡፡ ነገር ግን የህዝባችንን አስተሳሰብ ይበልጥ ለማጎልበት ግልፅ የውይይት መድረኮች ቢኖሩ፣ በዚያውም ላይ የእምነቱ አስተማሪዎች ለህዝባቸው ጥፋቱን የሚኮንኑበት አልፎም እውነቱን ግልፅ የሚያደርጉበት ሁኔታ ቢኖር መልካም ነው ባይ ነኝ፡፡
  2. ከዚህም ባለፈ ጉዳዩ ሰሞንኛ ብቻ እንዳይሆን የዚህ አይነቱን ጠርዘኛ አካሄድ በተመለከተ በሚደረገው የመፍትሄ ማፈላለግ ስራ ላይ ንቃት ያላቸው፣ እንደ አሕባሽ ያሉ ህዝብ ዘንድ የተተፉ ሳይሆኑ ሙስሊሙ ጆሮውን የሚሰጣቸው አስተማሪዎች ትርጉም ባለው መልኩ ተካፋይ ሊሆኑ ይገባል፡፡
  3. የሚዲያ ሰዎችም እንዲሁ ሀላፊነት ባለው፣ በተረጋጋና አሳታፊ በሆነ መልኩ እውነቱን ሊጋፈጡት የግድ ይላቸዋል፡፡
  4. ህዝባችንም አልፎ አልፎ እንደሚስተዋለው ምንም የማይገናኙ ነገሮችን እንደ ፂም፣ ልብስ ማሳጠር እና ኒቃብ መልበስ ያሉ ኢስላማዊ መገለጫዎችን ከሽብር ምልኮቶች ጋር በማቆራኘት ሰዎችን በሌሉበት ከማሸማቀቅ ሊርቅ ይገባል፡፡ ይሄ ከምንም በላይ ከሁሉም አቅጣጫ አጉል ድምዳሜ ላይ ያደርሳል፡፡
  5. ከዚህ ባለፈ በጦር ሜዳ ውሎ ላይ ስላሉ ክስተቶች የሚያትቱ የቁርኣንና የሐዲሥ ጥቅሶችን በተሳሳተ መንገድ፣ የእምነቱ አስተማሪዎች ከሚተነትኑት በተለየ ሁኔታና ተንኳሽ በሆነ መልኩ የሚተነትኑ አካላት አካላሄዳቸው ለማንም ስለማይበጅ ከዚህ ድርጊታቸው እንዲታቀቡ የቻልነውን ሁሉ ልናደርግ ይገባናል፡፡
  6. ሙስሊም የሃይማኖት አስተማሪዎች በየአጋጣሚው እንዲህ አይነቱን ድርጊት አጥብቀው ሊኮንኑ እንዲሁም በእምነቱ ቦታ እንደሌለውም ሊያስረዱ ሃላፊነት አለባቸው እላለሁ፡፡
    ከስራ መሃል ሆኜ ስለፃፍኩት ብዙ የሀሳብ መንዛዛት እንደሚኖረው ይሰማኛል፡፡ አላህ ሁላችንንም እውነቱን ያሳየን፡፡ አጥፊዎቹንም ወይ ልቦና ይስጣቸው፣ ወይ ጀርባቸውን ሰብሮ ይገላግለን፡፡

ሰላም

Ibnu Munewor

Print Friendly, PDF & Email

60

SHARES
Share on Facebook
Tweet
Follow us
Share
Share
Share
Share
Share

Filed Under: Opinions Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • ጃዋርና በቀለ መታሠራቸው ተሰማ June 30, 2020 09:17 am
  • አገራዊ መድረክ ውጪ ድብቅ ውይይትን አንቀበልም June 17, 2020 06:57 am
  • ዴክሳሜታሶን! የኮሮና መድሀኒት June 17, 2020 06:49 am
  • የሰኔ 14ቱ ቀለበታዊ የፀሃይ ግርዶሽ በኢትዮጵያ! June 17, 2020 06:38 am
  • የግብፅ የአባይን ውሃ ብቻዬን ልጠቀም ግትር አቋም ድርድር እንቅፋት ሆኗል June 10, 2020 07:15 am
  • የቴድሮስ “ሥልጣን” – የመጨረሻው መጀመሪያ!? April 12, 2020 02:48 am
  • በብዛት የትግራይ ተወላጆች የሚጠቀሙበት የኤርትራ ስደተኛ ካምፕ ሊዘጋ ነው March 18, 2020 08:37 pm
  • እየተፈረካከሰ ያለው አንጋፋው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ March 18, 2020 08:09 pm
  • ኮሮና አዲስ ጉድ መዘዘ – ከቻይና በፊት በአሜሪካ ቁጥራቸው የማይታወቅ ሰዎችን ቀጥፏል March 16, 2020 11:41 pm
  • የኮንዶሚኒየም ቤቶች በደላሎችና በመመሪያ ሰጪዎች ኔትዎርክ እየተቸበቸበ ነው! ታከለ የት ናቸው? March 9, 2020 10:18 am
  • ኤርሚያስ ለገሠ ከባለአደራ ተባረረ March 9, 2020 08:09 am
  • ድፍድፍ ሲቀል ይንሳፈፋል፤ ምሁር ሲዘቅት ይመራል፥ March 7, 2020 11:24 pm
  • ኢትዮጵያዊ ምን ይመስላል? በምንስ ይመሰላል? March 7, 2020 10:29 pm
  • WHY I WROTE “MONEY, BLOOD AND CONSCIENCE” March 4, 2020 11:15 pm
  • አድዋ፤ የጥቁር ሕዝብ ድል! March 2, 2020 11:24 am
  • ፊታውራሪ ገበየሁ ገቦ (አባ ጎራው) March 2, 2020 11:12 am
  • የኦነግ ሁለት መልክና ሦስት ግብሮች – ቃርሚያው ኃይል ቅጥር ነፍሰገዳይ ሆኗል February 25, 2020 11:26 pm
  • በቡራዩ “የጃል ማሮ” ፎቶ ጨረታ አፈናከተ፤ “ቡራዩ ሆኖ ከሃዲን ማሞካሸት አይቻልም” ነዋሪዎች February 17, 2020 09:13 pm
  • “ዲቃላ” የፍረጃ ፖለቲካ በኦሮሚያ የኃይል አሰላለፉን እየቀየረ ነው February 13, 2020 11:58 pm
  • “ከዚህ በኋላ ማናቸውንም በወንጀል ድርጊት ውስጥ የሚሳተፉ አካላትን” አንታገስም – ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ February 13, 2020 05:07 pm
  • “እኛ ማንም ተሳዳቢ እንዲመጣብን አንፈልግም” የጅማ ነዋሪ February 13, 2020 09:28 am
  • “ወላጆቻችሁ ሰላማዊ ሰልፍ በሕዝቡ ያስደርጉልን” – አጋቾች February 11, 2020 07:53 pm
  • “ወንጀል የፈጸመም ያስፈጸመም ተይዞ ለህግ ይቀርባል፤ ምርመራም ተጀምሯል” February 11, 2020 06:59 pm
  • ጃዋር ወደ መጨረሻው “የትግል” ስልቱ – አማራን ማበጣበጥ! February 10, 2020 11:54 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2026 · Goolgule