• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

መስከረም፣ መስከረም

September 16, 2017 01:57 am by Editor 2 Comments

ኢዮሃ አበባዬ / መስከረም ጠባዬ
ኢዮሃ አበባዬ / መስከረም ጠባዬ …

የወራት ሁሉ ቁንጮ መስከረም። ግንቦት እሳት፣ ሰኔ ውኃ ነው። የኢትዮጵያ ምድር በእሳትና በውኃ ሳትጠመቅ እረፍት እና ልምላሜዋን አታጋራም። ከግንቦት ማብቂያ እስከ መስከረም መጀመሪያ ሦስት ወር ብቻ ቢሆንም፣ እስኪጠባ መጠበቁ ሦስት ዓመት ያስመስለዋል። የመከራ አንዱ ቀን እንደ ዘላለም ነው፤ እግሮቹም በብረት ሰንሰለት ከብደዋል። ደስታ ግን ክንፍ እንጂ እግር የለው።meskerem1

ግንቦት ድርቅና ብክነት ነው። መስከረም እረፍትና ልምላሜ። ወራት መኳንንት ቢሆኑ መስከረም ንጉሥ ነው። መስከረም ደጅ ያስጠናል። ደጁን ካልከፈተ፣ ፊት ከነሳ ጥቅምትን ማየት አይቻል። አስራ ሁለቱን ወር እንደ ምን ተንፏቆ የደረሰ፣ አምስት እና ስድስት ቀን ጨምሮ ደጅ ይጠናል፤ ራሱንና ጓዳውን እንዲያዘገጃጅ ይገደዳል።

ይህን ያህል ርቀት ተጕዘው ለጥቂት ከደጅ የሚቀሩ አሉ። የሰኔ ጎርፍ ጠርጎ ወሰዳቸው የተባሉ ነፍስና ሥጋቸውን በጥርሳቸው አንጠልጥለው የሐምሌና የነሐሴን ሙላት ተሻገሩ። ሌላው ዳር ቆሞ የደረሱለትንና ያልደረሱለትን ምኞቶቹን ይከልሳል፤ ያመላልሳል። ሆያ ሆዬ ይላል። ሙልሙል ይጎረድማል።

እንደ ሞት ብቅ ይላል፤ መስከረም ሳይታሰብ ብቅ ይላል፤ እንዳላስጠበቀ ሌቱን ገስግሶ ከተፍ ይላል። ያለፈውን ዘመን አስረጅቶ ቀብሮ፣ አዲስ ሕይወት አዲስ ተስፋ ደግሶ ይቀበላል። “ሕይወት እነሆ!” ይላል።

መስከረም፣ እንቁጣጣሽ እንቁጣጣሽ ይላል፤ ጉዝጓዝ ሣር ትኵስ ቡና ይሸታል። እንኳን ደህና መጣሽ። ዓመት ዓመት ያምጣሽ፣
ኢዮሃ አበባዬ / መስከረም ጠባዬ
ኢዮሃ አበባዬ / መስከረም ጠባዬ
መስከረም ሲጠባ
ወደ አገሬ ልግባ …

የግንቦት ሕጻናት ቢይና አፈር ያቦናሉ፣ አፈር ያፍሳሉ፤ ንፍሮና ቆሎ ያፍሳሉ፤ ጠግበው ቁቅ ይላሉ። የመስከረም ሕጻናት እሸት እሸት ይሸታሉ፤ ያስገሳሉ። ቄኪያቸውን ሰው አፍ ላይ ይስላሉ። አበባ ይስላሉ። አደይ አበባ ይለቅማሉ። ወረቀት ያቀልማሉ፤ ለክርስትና አባታቸው ለክርስትና እናታቸው ለሚወዱት አያታቸው ለሚያቀብጣቸው አጎታቸው ለአክስታቸው ለጎረቤታቸው ያበረክታሉ። ስሙኒ ይለቅማሉ። ሜንታ ከረሜላ ይመጠምጣሉ፤ በደስታ ከረሜላ ይደሰታሉ። ቼሬአሊያ ይኮረሽማሉ፤ ጮርናቄ ያላምጣሉ። ይሳሳቃሉ። እንደ ተርብ ይሯሯጣሉ። ግንባር ለግንባር ተላትመው ይላቀሳሉ። ይንከባለላሉ። ይንቦጫረቃሉ። ስሙኒአቸውን ደጋግመው ይቆጥራሉ። ከሸመቱበት ወዲህ ፍራንኩ ማቃጨሉ ለምን እንደ ቀነሰ በጥርጣሬ ያሰላሉ።

ከሐምሌና ከነሐሴ ጎርፍ የተረፉ ይሰባሰባሉ። በየቤቱ በየቤተክርስቲያኑ ይሰባሰባሉ። በየአደባባዩ ይጨፍራሉ። አክ እንትፍ ያበዛሉ። ይገባበዛሉ። ይጎራረሳሉ። በሞቅታ ይንገዳገዳሉ። ይደጋገፋሉ። ሰላምታ ይሰጣጣሉ። ተስፋ ይቀባበላሉ፤ ተስፋ እንደ ማይጉም ይቀባባሉ። መስከረም ደስታ ነው፤ ልምላሜ ነው፤ ንጹሕ አየር ነው፤ ጤና ነው፤ ንቁ እርጥብ ፀሐይ ነው፤ ሰማያዊ ሰማይ ነው፤ የተባዘተ ጥሩ ጥጥ ብሩህ ደመና ነው። ብርሃንም እንደ ዝናብ፣ በታጨደ መስክ ላይ፥ በምድርም ላይ እንደሚንጠባጠብ ጠብታ ነው። የሚካበድ የአድማሳት ጥቁር ቡልኮ ወልቆ፣ እንቅልፍ የሚያስይዝ የሰላምና የሲሳይ ዝናብ ነው። ሰማይ የሚሰነጥቅ ጋራ የሚንድ የነጎድጓድ ድምጽ በወፎች ዝማሬ ሲተካ ነው። የደስታ ጅራፍ የሚያስያነጭ፣ የገደል ማሚቶ ኵልል ብሎ የወጣበት ጤዛ የሚያስመርቅ። መስከረም፣ ዳዊት የሚያስደግም ወር ነው፣

ምድርን ጎበኘሃት፣ አጠጣሃትም / ብልጥግናዋንም እጅግ አበዛህ
የእግዚአብሔር ወንዝ ውኃን የተመላ ነው / ምግባቸውን አዘጋጀህ፣ እንዲሁ ታሰናዳለህና
ትልምዋን ታረካለህ / ቦይዋንም ታስተካክላለህ
በነጠብጣብ ታለሰልሳታለህ / ቡቃያዋንም ትባርካለህ
በቸርነትህ ዓመትን ታቀዳጃለህ / ምድረ በዳውም ስብን ይጠግባል
የምድረ በዳ ተራሮች ይረካሉ / ኮረብቶችም በደስታ ይታጠቃሉ
ማሰማርያዎች መንጎችን ለበሱ / ሸለቆችም በእህል ተሸፈኑ
በደስታ ይጮኻሉ፣ ይዘምራሉም። [ዳዊት 65፡9-13]

meskerem2ደጁን አንኳኵተው ለከፈተላቸው መስከረም ግብዣው ብዙ ነው፤ ድግሱ የጦፈ። የጋመ በቆሎ እሸት ጥብስ። ቅቤ ልውስ አንጮቴና ቡና ቀላ። ትኵስ አቦል ቡና ቅቤ በረካ። በአስራ ሁለት የጉራጌ መስቀል፣ በአስራ ስድስት ደመራ፣ በአስራ ሰባት ለተቀረነው መስቀል። ጠፍቶ የከረመው የሚገኝበት፣ እሳትና ዐመድ የተስማማበት። ግንቦት በፀሐይ እሳት ያቦነነውን፣ መስከረም በደመና እሳት አብርዶ ያሳርገዋል።

በአስራ ስምንት፣ ተማሪ ልብሱን አጥቦ ተስፋ ፍለጋ፣ እውቀት ፍለጋ ደብተሩን ይዞ ይራመዳል። ከጳጉሜ [ጳጉሜን፣ ቋቍሜ] መስከረም እስኪሸኝ፣ የአገር ሰላምታ እንደ በረቅ እንደ ነጎድጓድ ከቅርብና ከርቀት ይንጎደጎዳል፤ እንደ ምንጭ ውኃ እንደ ጅረት ይዥጎደጎዳል፦
እንኳን አደረሰህ … እንኳን አደረሰሽ
እንኳን አደረሰሽ … አሜን እንኳን አደረስዎ
እንኳን አደረሰዎ … እንኳን አደረሰሽ
እንኳን አደረሳችሁ … እንኳን አደረስዎ አባባ
ሃፒ ኒው ይር ማዘር … ሃቢኑር ያርግሽ እቴ፣ እንኳን አደረሰሽ በዪልኝ እናትሽን
አደረሳችሁ … ይመስገነው … ክብሩ ይስፋ…

meskerem3መስከረም የወሮች ሁሉ ንጉሥ ነው። የኢትዮጵያ ክልሎች፣ ወረዳዎች፣ አደባባዮች፣ ቀዬዎች እና ጓዳዎች ይዘጋጁ፤ ከሩቅ እጅ ይንሱ፣ ከቅርብ እጅ ይንሱ። የሰላም እሳት ያጋዩ፣ ያደፈውን እና ያረጀውን ያቃጥሉ። የመስቀሉ እሳት ተውሳኩን ያጋይ! የአጋንንትን መንጋ ያክስም። የተስፋ ችቦ ይብራ። በአንድነት ሆ! ይበሉ። የደስታ ሆታቸውን ሸለቆ ሸንተረሩ ጋራና ፈፋው ተቀብሎ ያስተጋባ። “ምነው ተሽኮረመምሽ? እንደ መስቀል ወፍ የት ጠፍተሽ ከረምሽ?” ይባባሉ።

ኢዮሃ አበባዬ / መስከረም ጠባዬ
መስከረም ሲጠባ / አደይ ሲፈነዳ
እንኳን ሰው ዘመዱን / ይጠይቃል ባዳ

ለተቀረው ዓለም፣ አዲስ ዓመት ጥር ነው። ለኛ አዲስ፣ መስከረም ነው።

የሰላምና የምህረት ዓመት ይሁንልን!

© ምትኩ አዲሱ፣ 2010 ዓ.ም

Image credit: skyscrapercity.com; googleimages.com


“ጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ የሕዝብ” እንደመሆኑ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ ሥር የድርጅቶችና የማንኛውም ግለሰብ ነጻ ሃሳብ የሚስተናገድ ሲሆን ከአንባቢያን የሚላኩልን ጽሁፎች በጋዜጣው የአርትዖት (ኤዲቶሪያል) መመሪያ መሠረት ያለ መድልዖ በዚህ ዓምድ ሥር ይታተማሉ፡፡ ይህ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ የታተመ ጽሁፍ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® አቋም ሳይሆን የጸሃፊው ነው፡፡

Print Friendly, PDF & Email

60

SHARES
Share on Facebook
Tweet
Follow us
Share
Share
Share
Share
Share

Filed Under: Opinions Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Comments

  1. Mulugeta Andargie says

    September 20, 2017 04:02 am at 4:02 am

    መስከረም!! መስክ አረም!! መስከረም!
    ያዲስ ዓመት ለምለም ወራት! ለምለም!
    ክረምት አላፊ ሃምሌ ነሃሴ!
    ዓዲስ ዓመቱ መጣ ፈሰሴ
    መስከረም ጠባ ወፎች ዘመሩ
    ቢጫው ዓደዩ ሲታይ ማማሩ!
    በየመኩ ላይ ተዘርቶ ፈክቶ
    እንደ መስከረም ማን አለ ከቶ??

    Reply
  2. Mitiku says

    October 1, 2017 12:18 am at 12:18 am

    ውድ ሙሉጌታ፣
    መስከሮምን አሳመርከው አደል? አንተም ይመርብህ!
    ምትኩ

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • ጃዋርና በቀለ መታሠራቸው ተሰማ June 30, 2020 09:17 am
  • አገራዊ መድረክ ውጪ ድብቅ ውይይትን አንቀበልም June 17, 2020 06:57 am
  • ዴክሳሜታሶን! የኮሮና መድሀኒት June 17, 2020 06:49 am
  • የሰኔ 14ቱ ቀለበታዊ የፀሃይ ግርዶሽ በኢትዮጵያ! June 17, 2020 06:38 am
  • የግብፅ የአባይን ውሃ ብቻዬን ልጠቀም ግትር አቋም ድርድር እንቅፋት ሆኗል June 10, 2020 07:15 am
  • የቴድሮስ “ሥልጣን” – የመጨረሻው መጀመሪያ!? April 12, 2020 02:48 am
  • በብዛት የትግራይ ተወላጆች የሚጠቀሙበት የኤርትራ ስደተኛ ካምፕ ሊዘጋ ነው March 18, 2020 08:37 pm
  • እየተፈረካከሰ ያለው አንጋፋው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ March 18, 2020 08:09 pm
  • ኮሮና አዲስ ጉድ መዘዘ – ከቻይና በፊት በአሜሪካ ቁጥራቸው የማይታወቅ ሰዎችን ቀጥፏል March 16, 2020 11:41 pm
  • የኮንዶሚኒየም ቤቶች በደላሎችና በመመሪያ ሰጪዎች ኔትዎርክ እየተቸበቸበ ነው! ታከለ የት ናቸው? March 9, 2020 10:18 am
  • ኤርሚያስ ለገሠ ከባለአደራ ተባረረ March 9, 2020 08:09 am
  • ድፍድፍ ሲቀል ይንሳፈፋል፤ ምሁር ሲዘቅት ይመራል፥ March 7, 2020 11:24 pm
  • ኢትዮጵያዊ ምን ይመስላል? በምንስ ይመሰላል? March 7, 2020 10:29 pm
  • WHY I WROTE “MONEY, BLOOD AND CONSCIENCE” March 4, 2020 11:15 pm
  • አድዋ፤ የጥቁር ሕዝብ ድል! March 2, 2020 11:24 am
  • ፊታውራሪ ገበየሁ ገቦ (አባ ጎራው) March 2, 2020 11:12 am
  • የኦነግ ሁለት መልክና ሦስት ግብሮች – ቃርሚያው ኃይል ቅጥር ነፍሰገዳይ ሆኗል February 25, 2020 11:26 pm
  • በቡራዩ “የጃል ማሮ” ፎቶ ጨረታ አፈናከተ፤ “ቡራዩ ሆኖ ከሃዲን ማሞካሸት አይቻልም” ነዋሪዎች February 17, 2020 09:13 pm
  • “ዲቃላ” የፍረጃ ፖለቲካ በኦሮሚያ የኃይል አሰላለፉን እየቀየረ ነው February 13, 2020 11:58 pm
  • “ከዚህ በኋላ ማናቸውንም በወንጀል ድርጊት ውስጥ የሚሳተፉ አካላትን” አንታገስም – ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ February 13, 2020 05:07 pm
  • “እኛ ማንም ተሳዳቢ እንዲመጣብን አንፈልግም” የጅማ ነዋሪ February 13, 2020 09:28 am
  • “ወላጆቻችሁ ሰላማዊ ሰልፍ በሕዝቡ ያስደርጉልን” – አጋቾች February 11, 2020 07:53 pm
  • “ወንጀል የፈጸመም ያስፈጸመም ተይዞ ለህግ ይቀርባል፤ ምርመራም ተጀምሯል” February 11, 2020 06:59 pm
  • ጃዋር ወደ መጨረሻው “የትግል” ስልቱ – አማራን ማበጣበጥ! February 10, 2020 11:54 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2026 · Goolgule