• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ቀጠሮ ይዣለሁ

May 23, 2014 01:06 am by Editor 1 Comment

እንደማንኛውም ባለቀጠሮ፤ ቀጠሮዬ ደርሶ፤ ከቦታው ተገኝቼ የማደርገውን የግሌን ጉዳይ እንጂ፤ “ሌላው” ጉዳይ አሁን አላስጨነቀኝም። “ሌላው” ያልኩት ትልቁ ጉዳይ፤ የቀጥሮዬ ቀን መቼ እንደሆነ፣ ለቦታው አደራረሴንና በዚያ ስደርስ የሚጠብቀኝን ነው። እነኚህ ለቀጠሮዬ ሕልውና ወሳኝ ቢሆኑም፤ በኔ ቁጥጥር ሥር ስላልሆኑ፤ ለጊዜው ወደ ጎን ገፋ አድርጌያቸዋለሁ። በተጨማሪም እኒህን ጉዳዮች ከናንተ ጋር የምጋራቸው ስለሆነ፤ አብረን እንድናቃናቸው ለሌላ ጊዜ ትቼ፤ በኔ ቁጥጥር ሥር ስላለውና በአእምሮዬ ስለሚዋልለው እንጨዋወት። ቀጠሮዬ ሀገሬ ኢትዮጵያ ለመግባት ነው። ኢትዮጵያ እስከሆነ ድረስ፤ የተወለድኩባትና ያባትና የናቴ አፅም ያረፈባት ጎንደር – አዘዞ ትሁን የተማርኩበትና ብዙ ጊዜ ያሳለፍኩበት አዲስ አበባ፤ ግድ የለኝም።

የሀገሬ የኢትዮጵያ ትዝታዬ፤ ብዙ ቦታ ይወሰደኛል። ጓደኞች ያፈራሁባቸው ቦታዎች፣ በአራት ዓመት ውስጥ ስንከራተት፤ ያስተማርኩባቸው ሁለተኛ ደረጃና አንደኛ ደረጃ ት/ቤቶችና ያሉባቸው ከተማዎች፣ (ከምባታ – ዋቸሞና ጢምባሮ – ግምቢቹ፣ ይፋትና ጥሙጋ – ደብረሲና፣ መናገሻ – አቃቂ፣ የረርና ከረዩ – ደብረዘይትና ግምቢቹ፣ ተመልሼ መናገሻ – ሰንዳፋ ) እህቴ በዕድገት በሕብረት ዘምታ ሄጄ የጠየቅኋትና ወደኔ ያመጣሁበት ሲዳማ – አለታ ወንዶ፣ በእናቴ የሚዘመዱኝን ልጠይቅ የሄድኩበት እስቴ – ቆማ ፋሲለደስ፣ በአባቴ የሚዘመዱኝን ልጠይቅ የሄድኩበት አዴት – ደብረመይ፣ ሁሉ በትዝታዬ ፊት ይንከራተታሉ። በ፲ ፱ ፻ ፷ ፮ ዓመት ምህረት ሰላማዊ ሰልፍ የወጣሁባቸው መንገዶች፣ በወቅቱ በትግሉ ዙሪያ ያሳለፍኩባቸው ቦታዎችና ያገኘኋቸው ሰዎች፤ በአእምሮዬ አብረውኝ አሉ። ለስደት ወደ ሱዳን የተንከራተትኩበት የአርማጨሆና የጭልጋ ምድር ሁሉ በአእምሮዬ እየተንከራተተ፤ ምንድን ነው ቀጠሮዬ? ምን አደርጋለሁ? ይኼን ነው እዚህ ላይ ያሰፈርኩ።

በአስተዳደጌ፤ ሀገር ምንነት ነው። እንደደም በሰውነቴ ውስጥ፣ እንደጥላ ከሰውነቴ ውጪ፣ ኢትዮጵያዊነቴ ሁሌም አብሮኝ አለ። እናም ኢትዮጵያን ከኔ አውጥቼ፤ ለኔም ሆነ ለሀገሬ ሕልውና መሥጠት አልችልም። ባደኩበት ኅብረተሰብ የኔን ሕልውና ትርጉም የሠጠሁት፤ የኅብረተሰቡ አካል አድርጌ ስለነበር፤ እኔን ከኅብረተሰቡ ለይቼ ዓይቼ አላውቅም። የኔን ሕልውና ከነበሩት ቀጣይና ለመጭዎቹ መሰላል አድርጌ ነው የማየው። ስለዚህ ምንም እንኳ አሁን ቀንድ ካበቀልኩ በኋላ በመጣሁበት ሀገር፤ ሁሉም “ለራሴ ነው የምኖር” ብሎ አማኝ ቢሆንም፤ እኔ አሁንም በግል መኖር ወይንም የኔን ሕይወት የራሴ የግሌ ብቻ አድርጌ አልወሰድም። እኔን እኔ በማድረግ በኩል፤ ከወላጆቼ ቀጥሎ፤ አካባቢዬና የሀገሬ ሰዎች በሙሉ አስተዋፅዖ አላቸው። ለዚህም ነው በኢትዮጵያዊያን ገንዘብ ሕልውናዬ ተጠብቆ፣ አድጌ፣ ተምሬ፣ በተማሪነቴ ታጋይ ሆኜ፣ ከዩኒቨርሲቲ ተባርሬ፣ ሥራም ይዤ አስተማሪ ሆኜ፣ የኖርኩ። ይህ የምንነቴ አምድ ነው። ከዚህ ውጪ እኔ የለሁም። እናም ማንነቴ ይኼ ነው። ለዚህ ሕይወቴን ታሣሪ አድርጌዋለሁ። እናም ይህ፤ ምን ጊዜም በምኞቴም ሆነ በሕልሜ የምመላለስበት የግል የአእምሮዬ ጓዳ ነው። አብረውኝ በትግል ዓለም ውስጥ ያለፉት አሁንም በኑሮዬ አብረውኝ አሉ። ለምን ይኼን ዓይነት ኑሮ እንደምኖርና ወደፊት ሀገሬን እንደምመኝ ግልፅ ነው።

ቀጠሮዬ ደርሶ ኢትዮጵያ ስገባ ምን አድርጋለሁ። በመጀመሪያ ደረጃ ቀጠሮዬ ደርሶ ኢትዮጵያ እንደምደርስ፤ ምንም ዓይነት ጥርጣሬ የለኝም። ዘንድሮ ለግንቦት አስራ አምስት አልደረስኩም። ለመጪው የ፳ ፻ ፮ ዓመተ ምህረት እንቁጣጣሽ ላልደርስ እችላለሁ። አዎ ራሱን “የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር” ብሎ ከሚጠራው መንግሥት ጋር ጠብ አለኝ፣ ትግራይን አልፎ ተከዜን ተሻግሮ ወልቃይት በገባ ጊዜ፤ ያኔ በነበርኩበት የድርጅት ሠራዊት አባል ሆኜ ጦርነት ገጥመን ቆስያለሁ። ይህ ወገንተኛና አምባገነን ቡድን በሥልጣን ላይ እያለ ሀገሬን ማየቴ አይታሰብም። እርግጠኛ ሆኜ የማምነው ግን፤ ውሎ አድሮ ፀሐይ ነገ መውጣቷ እንደማይቀር ሁሉ፤ ይህ ቡድን ይወድቃል፤ እኔም ሀገሬን አያለሁ። ብቻዬን ደግሞ አይደለሁም። የተለያዬ የግል መንገድ ቢኖረንም፤ ከሞላ ጎደል በዚሁ ጥላ ሥር ያለን ብዙዎች ነን።

የምመለስባት ኢትዮጵያ ከነበርኩባት ኢትዮጵያ የተለየች እንደምትሆን ጥርጥር የለኝም። ሕይወቴን በሙሉ የታጋልኩለት የሕዝቡ ዴሞክራሲያዊ መብት መከበር ሀቅ የሆነባት ኢትዮጵያ ትሆናለች። የእያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ መብት በሕግና በተግባር የተጠበቀባት ትሆናለች። የሕግ የበላይነት የሠፈነባት ትሆናለች። የሕዝቡ ሉዓላዊነት ያላንዳች ማቅማማት የተረጋገጠባት ትሆናለች። መቼም እንደኔ ከሀገሩ የወጣ ሁሉ፤ የሀገራችን የኢትዮጵያ መሪ አይሆንም። ሁሉም የኢትዮጵያ ሚኒስቴርና የኢትዮጵያ አምባሳደር አይሆንም። ሁሉም የአዲስ አበባ ባለሕንፃ አይሆንም። ሁሉም በዘመናዊ መኪና ተንፈላሳሽ አይሆንም። ሁሉም በለሙ የኢትዮጵያ መሬት ባለሠፊ እርሻ አይሆንም። ሁሉም ነጋዴ አይሆንም። ሁሉም የኢትዮጵያ የእግር ኳስ ተጫዋች አይሆንም።  እያንዳንዱ የራሱ የሆነ የተማረበት፣ የሠለጠነበትና ልምድ ያካበተበት ሙያ ይዞ እንደሚገባ እርግጠኛ ነኝ። በዚህም ሀገራችንን ኢትዮጵያን ብዙ ወደፊት እንደምናራምዳት ቅንጣት ታክል ጥርጥር የለኝም። እናም ቀጠሮ የያዝኩት ለዚህ ነው።

በቅርቡ እናቴን በቦታው ተገኝቼ ልቀብራት አልቻልኩም። መቃብሯን ሄጄ አያለሁ። ቦታው ባንድ ላይ በሆነው ባባቴ መቃብርም፤ ብዙ ጊዜ እየተመላለስኩ ለማየት ዕቅድ አለኝ። የጠለምትን ውጣ ውረድ እሄድበታለሁ። በደሴ አልፌ አሲምባ – ስንገደን መጎብኘት እወዳለሁ። ወልቃይት ጠገዴን በየመንደሩ እየሄድኩ ሰዎችን ማግኘት፤ ቦታውን መቃኘት እፈልጋለሁ። ኑሮዬን የት እንደማደርግ ቁርጥ ያለ ዕቅድ ባይኖረኝም፤ ሀገራችን ብዙ የተለያየ ሙያ ያላቸው ሰዋች እንደሚያስፈልጋት ስለምረዳ፤ ባንዱ የሙያ ዘርፍ ገብቼ ወገኔን እንደማገለግል ጥርጥር የለኝም። ተማሪ ነበርኩ መምህር ነበርኩ፤ ዋናው ካገሬ ያወጣኝና በውጭ እንድቆይ ያደረገኝ ለሕዝቡ ዴሞክራሲያዊ መብት መታገሌ ነውና፤ ይህ ሲተገበር፤ ራሱ በቦታው ሆኖ ማየቱ፤ የመኖሬን ትርጉም ተጨባጭ ያደርገዋል። እናም በጣም እጓጓለሁ። እዚህም ትንሽ ተምሬ ሙያ አካብቻለሁ። ልምድም ሸምቻለሁ።

ሰዎችን ወደፊት እንዲመለከቱ የሚያደርጋቸው ተስፋ ነው። ተስፋ ደግሞ መነሻው ተጨባጭ የሆነ ክስተት አለው። ወደ ሀገሬ ተመልሼ ለመሄዴ ተስፋዬ፤ አሁን በሀገራችን ያለው የዴሞክራሲ ጥማትና የታጋዩ ብዛት ነው። በዞን ዘጠኝ አርበኞች ምን ያህል እንደምኮራና እንደምቀናባቸው የልቤን አውጥቼ ልናገር ብል፤ መግለጫ ቋንቋው አይበቃኝም። በምንም መንገድ ቢተረጎም ሁላችን የምንፈልገው፤ ረሃብን ከሀገራችን አስወግደን፣ በሺታን በቁጥጥር ሥር አውለን፣ እያንዳንዷ ኢትዮጵያዊት በሀገሯ የትም ሠርታ የመኖር መብቷ ገደብ ሳይኖርበት፣ ሀብት ለማፍራትና ትዳሯን ለመመሥረት አዛዥ ሳይጫናት፣ ልማትና ትምህርት የተሥፋፉባት ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ ነው። ይህ ዋናው ዕሴታችን ነው። ይህ በተግባር ላይ ይውላል። ያኔ ዞረን ብዙ ነገሮችን እንቃኛለን። ያኔ የየራሳችንን ፓርቲዎች በሕዝቡ ፊት እያቀረብን እንወዳደራለን። በቃኝ ብዬ የማልተወው ነገ ቢኖር፤ አሁን ፓርቲ ባይኖረኝም ከሚስማማኝ ጋር ተላትሜ፤ በሀገሬ የፖለቲካ ምኅዳር ተካትቼ ዴሞክራሲያዊ መብቴን መጠቀምና፤ ተሳትፎ ማድረግ ነው። ያኔ ያንድ ቡድን አዋቂነትና ብቸኛ ገዥነት በመጽሐፍ የሚነበብ ይሆናል። የሕዝቡን ሉዓላዊነት በተግባር እንረዳለን። ያኔ መምህሮችና ተማሪዎች እንሆናለን። ከዚያች ቀን ጋር ቀጠሮ ይዣለሁ።

ያኔ በየትኛውም የሀገራችን ኢትዮጵያ ክፍል የሚኖሩ ኢትዮጵያዊና ኢትዮጵያዊት ሁሉ፤ አባታቸው ማነው? እናታቸው ማናት? ደማቸው ከየትኛው ወንዝ ይቀዳል? ምን ቋንቋ ይናገራሉ? ሃይማኖታቸው ምንድን ነው? ስንተኛ ክፍል ድረስ ተምረዋል ሳይባል፤ ሁሉም እኩል ኢትዮያዊና ኢትዮጵያዊት፤ እኩል መብት ያላቸው ይሆናሉ። በሕግ ፊት ሁሉም እኩል ይታያሉ። የሀገሪቱ መሪ እንደኔ እኩል ከፍርድ ፊት ይቀርባል/ትቀርባለች። ያኔ ኢትዮጵያዊነት ይከበራል። ያኔ የሃይማኖት ነፃነት በገሃድ ይታያል። ያኔ የማመንም ሆነ ያለማመን፣ የራሱን ፈጣሪ የመሰየምም ሆነ በተሰየመው ለመካተት፤ ሁሉም መብት ይኖረዋል። ያኔ የግል ማንነትን ራሱ ግለሰቡ እንጂ ማንም ሊተረጉምለት እንደማይችል ሕጉ ይደነግጋል። ያኔ በኢትዮጵያ ምድር እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊና እያንዳንዷ ኢትዮጵያዊት በግለሰብ ኢትዮጵያዊት ብቻ የፖለቲካ ተሳትፏቸውን፣ የሥራ ተግባራቸውን፣ የንግድ ስምሪታቸውን ያከናውናሉ። በትምህርት መስክም ሆነ በውትድርና፣ በተቀጣሪነትም ሆነ በቀጣሪነት፤ ኢትዮጵያዊነት ብቻ ይሆናል መለኪያው። ለዚያ ቀን ቀጠሮ ይዣለሁ።

ያ ብቻ አይደለም። ልቤ ትልቅ ነው። በያንዳንዱ የስፖርት ዘርፍ ግንባር ቀደም ከሚሠለፉት ሀገሮች መካከል ኢትዮጵያ ትገኛለች። ያኔ የሚወለዱ ልጆች ረሃብንና በሽታን በታሪክ መጽሐፍት ብቻ ነው የሚያውቋቸው። ያኔ አረንጓዴ ብጫና ቀይ ቀለም ያለው የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ በየቦታው ሲውለበለብ ልባችን በደስታ ይፈነድቃል። በኒው ዮርክ ማራቶን፣ በፊፋ የዋንጫ ሽልማት ጊዜ ሁሉም ኢትዮጵያዊ ትንንሽ አረንጓዴ ብጫና ቀይ ስንደቅ ዓላማውን አንስቶ፤ ሌሊቱ እንዳይጨልም ይሟገታል። የሳይንስ ሊቆች፣ የሕክምና ፈላስፎች፣ የምርምርና ጥናት አዋቂዎች በየመንገዱ ይታያሉ። ለሙ ያገራችን መሬትና ያገራችን ሆድ ዕቃዎች፣ የምርት መዛቂያ ይሆናሉ። ለዚያ ቀን ቀጠሮ ይዣለሁ።

በነገራችን ላይ፤ አብሮ ከኔ ጋር ቀጠሮ ላማድረግ ለሻ ሁሉ፤ ወጪያችንን ለመጋራትና ለመተባበር ዝግጁ ነኝ።

eske.meche@yahoo.com

Print Friendly, PDF & Email

60

SHARES
Share on Facebook
Tweet
Follow us
Share
Share
Share
Share
Share

Filed Under: Opinions Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Comments

  1. bezabih molla says

    May 28, 2014 02:51 pm at 2:51 pm

    አለን ከጎንህ ነን በርታ እድሜየን በሙሉ ነፃነቴን አጥቻለሁ

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • ጃዋርና በቀለ መታሠራቸው ተሰማ June 30, 2020 09:17 am
  • አገራዊ መድረክ ውጪ ድብቅ ውይይትን አንቀበልም June 17, 2020 06:57 am
  • ዴክሳሜታሶን! የኮሮና መድሀኒት June 17, 2020 06:49 am
  • የሰኔ 14ቱ ቀለበታዊ የፀሃይ ግርዶሽ በኢትዮጵያ! June 17, 2020 06:38 am
  • የግብፅ የአባይን ውሃ ብቻዬን ልጠቀም ግትር አቋም ድርድር እንቅፋት ሆኗል June 10, 2020 07:15 am
  • የቴድሮስ “ሥልጣን” – የመጨረሻው መጀመሪያ!? April 12, 2020 02:48 am
  • በብዛት የትግራይ ተወላጆች የሚጠቀሙበት የኤርትራ ስደተኛ ካምፕ ሊዘጋ ነው March 18, 2020 08:37 pm
  • እየተፈረካከሰ ያለው አንጋፋው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ March 18, 2020 08:09 pm
  • ኮሮና አዲስ ጉድ መዘዘ – ከቻይና በፊት በአሜሪካ ቁጥራቸው የማይታወቅ ሰዎችን ቀጥፏል March 16, 2020 11:41 pm
  • የኮንዶሚኒየም ቤቶች በደላሎችና በመመሪያ ሰጪዎች ኔትዎርክ እየተቸበቸበ ነው! ታከለ የት ናቸው? March 9, 2020 10:18 am
  • ኤርሚያስ ለገሠ ከባለአደራ ተባረረ March 9, 2020 08:09 am
  • ድፍድፍ ሲቀል ይንሳፈፋል፤ ምሁር ሲዘቅት ይመራል፥ March 7, 2020 11:24 pm
  • ኢትዮጵያዊ ምን ይመስላል? በምንስ ይመሰላል? March 7, 2020 10:29 pm
  • WHY I WROTE “MONEY, BLOOD AND CONSCIENCE” March 4, 2020 11:15 pm
  • አድዋ፤ የጥቁር ሕዝብ ድል! March 2, 2020 11:24 am
  • ፊታውራሪ ገበየሁ ገቦ (አባ ጎራው) March 2, 2020 11:12 am
  • የኦነግ ሁለት መልክና ሦስት ግብሮች – ቃርሚያው ኃይል ቅጥር ነፍሰገዳይ ሆኗል February 25, 2020 11:26 pm
  • በቡራዩ “የጃል ማሮ” ፎቶ ጨረታ አፈናከተ፤ “ቡራዩ ሆኖ ከሃዲን ማሞካሸት አይቻልም” ነዋሪዎች February 17, 2020 09:13 pm
  • “ዲቃላ” የፍረጃ ፖለቲካ በኦሮሚያ የኃይል አሰላለፉን እየቀየረ ነው February 13, 2020 11:58 pm
  • “ከዚህ በኋላ ማናቸውንም በወንጀል ድርጊት ውስጥ የሚሳተፉ አካላትን” አንታገስም – ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ February 13, 2020 05:07 pm
  • “እኛ ማንም ተሳዳቢ እንዲመጣብን አንፈልግም” የጅማ ነዋሪ February 13, 2020 09:28 am
  • “ወላጆቻችሁ ሰላማዊ ሰልፍ በሕዝቡ ያስደርጉልን” – አጋቾች February 11, 2020 07:53 pm
  • “ወንጀል የፈጸመም ያስፈጸመም ተይዞ ለህግ ይቀርባል፤ ምርመራም ተጀምሯል” February 11, 2020 06:59 pm
  • ጃዋር ወደ መጨረሻው “የትግል” ስልቱ – አማራን ማበጣበጥ! February 10, 2020 11:54 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2026 · Goolgule