• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ሰውና ልማት

July 25, 2014 09:04 pm by Editor Leave a Comment

ሰው በእግዚአብሔር አምሳል የተፈጠረ ነው፤ ሕይወቱ ክቡር ነው፤ ክቡር ሕይወቱን ለመጠበቅ ብዙ ፍላጎቶቹን ማሟላት አለበት፤ አንዳንዶቹ ፍላጎቶች በየዕለቱ የሚከሰቱና የሚጎተጉቱ ናቸው፤ ስለዚህም ወዲያው ካልተስተናገዱ በጤንነት ላይ መጥፎ ውጤትን ያስከትላሉ፤ምግብና መጠጥ ግዴታዎች ናቸው፤ ልብስና መጠለያም ግዴታዎች ናቸው፤ ሰው ሁሉም ነገር ከተሟላበት ከገነት ከተባረረ በኋላ በግንባርህ ላብ ብላ ተብሎ ተረግሟል፤ በሰላም በሕግ ጥላ ስር የመተዳደር ፍላጎትም አለ፤ በአለው አቅምና ችሎታ አነዚህን ፍላጎቶች ለማሟላት ይጥራል፤ ይህ ቀላል አይደለም፤ ቀላል የማያደርጉት ብዙ ምክንያቶች አሉ።

አንደኛ፣ የሰውም፣ የእንስሳም፣ የእጸዋትም ሁሉ መኖሪያና መመገቢያ ምድር አንድ ነች፤ ስለዚህ ውድድሩ ከባድ ነው፤ በዚች ምድር ላይ እየኖሩ፣ ምድር የምታፈራውን እየተመገቡ፣ ውሀዋን እየጠጡ በሰላም መኖር አይቻልም፤ የሰው ልጅ ከቢምቢ ጋር ብቻ ሳይሆን ከሰው ቢምቢ ጋርም መታገል አለበት፣ ከዱር አንበሳ ጋር ብቻ ሳይሆን ከሰው አንበሳ ጋርም ነው።

ሁለተኛ፣ ፍላጎቶች የሥራ ሁሉ ምንጭ ስለሆኑ በጣም ይራባሉ፤ የመራባት አቅማቸው ከሰው ልጅ መራባትና የመፍጠር ችሎታ ጋር የተያያዘ ነው፤ በተጨማሪም ለተመቸው ሁሉ አምሮቶች ፍላጎቶች ይሆናሉ፤ ደሀዎችንና ሀብታሞችን የሚለየው አንዱ ዋና ነገር የፍላጎቶች ብዛት ነው፤ የደሀ ፍላጎቶች ከመሠረታዊ ፍላጎቶች አይርቁም፤ የሀብታሙ ፍላጎቶች ከትልቅ ቤት ወጥተው በትልቅ መኪና አድርገው በአውሮጵላን ሰማይ ይወጣሉ፤ ከዚያም አልፈው ይቧጭራሉ።

ሦስተኛ፣ በፍላጎቶች መራባት ላይ አምሮት ታክሎበት፣ እነዚህን ፍላጎቶችና አምሮቶች ማስተናገድና ማርካት ከባድ ፉክክርን ይፈጥራል፤ አብዛኛውን ጊዜ በፉክክር ላይ የሚታየው የተሠራው ቤት ትልቅነትና ውበት፣ የታረደው ሙክት ትልቅነትና ስብነት፣  የሚለብሰው ልብስ ስፌትና ውበት፣ የሚነዳው መኪና ዓይነት የሰዎቹን የኑሮ ደረጃ ያሳያል፤ በግለሰብ ደረጃ ይህ ከፍተኛ የልማት ደረጃን ያመለክታል፤ የግለሰቦችን እድገት የሚጠላ የለም፤ ጥያቄው የግለሰቦች አድገት በምን ዓይነት መንገድ ተገኘ ነው፤ ግለሰቦች በሕገ-ወጥ መንገድ ደሀውን እያሠሩና እያፈናቀሉ መሬቱን በዝርፊያና በቅሚያ ሌሎቹን እያደኸዩ ራሳቸውን የሚያበለጽጉ ነገን የማያስቡ ዕለትዋን ዘለዓለም አድርገው የሚቀበሉ ግዴለሾች፣ ወይም ጅሎች ናቸው።

ethio poorበግፍ የበለጸጉ በግፍ ይደኸያሉ፤ ትናንት መንግሥቱ ኃይለ ማርያም በአንድ ቀን ስንቱን ሀብታም ባዶ እንዳደረገውና እንዳኮማተረው ይህ ትውልድ አላየም፤ ግን ሰምቷል፤ በደርግ ዘመን የመሬት አዋጁንና የትርፍ ቤቶች አዋጆች ያስከተሉትን ሐዘንና ድንጋጤ ያዩ ሰዎች እንዴት እንደገና ሊመጣ ይችላል ብለው ማሰብ ያቅታቸዋል? አንዱ የመክሸፍ ዝንባሌ እንዲህ በቅርቡ የሆነውን መርሳትና ምንም ትምህርት ሳያገኙበት ኑሮን እንደዱሮው መቀጠል ነው፤ ታሪክ የሚከሽፈው እንዲህ ትምህርት መሆን ሲያቅተው ነው፤ በየመንገዱ፣ በየቀበሌው በየስብሰባው ጥርሱን እየነከሰ የውስጥ ቁስሉን የሚያሽ ሰው ሞልቷል፤ የሚራገም ሰው ሞልቷል፤ ከተወለዱበት፣ ከአደጉበትና ለስድሳ ዓመት ከኖሩበት፣ ሠርግና ተዝካር ከደገሱበት ሰፈር ተገድዶ መልቀቅ፣ በልጅነት አብረው እየተጫወቱ፣ በኋላም በትምህርት ቤት አብረው በጓደኝነት ከዘለቁ፣ በሥራ ዓለም ከገቡ በኋላ በቅርብ ወዳጅነት አብረው ከቆዩ፣ በአንድ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን በሃይማኖት በዓላት በደስታም በሐዘንም ከሃምሳ ዓመታት በላይ ያልተለያዩ ሰዎች ጉልበተኛ መጥቶ በግድ ሲበትናቸውና ሲለያዩ፣ መድኃኔ ዓለም ይበትናችሁ! ሳይሉ ይቀራሉ? በግፍ የበለጸጉ በዚህ እርግማን እየተበተኑ ይደኸያሉ፤ እግዚአብሔር በቀዳዳው ያያል፤ አትጠራጠሩ!

ሰውን ገድሎ በሬሣው ላይ ቤት ሠርቶ ሀብታም መሆን ልበ-ደንዳኖች ለአጭር ሕይወታቸው የሚጠቀሙበት ከንቱ ድሎት ነው፤ ሕገ-ወጥነት ነው፤ ግዴለሽነት ነው፤ በቅርቡ ኤርምያስ እንደነገረን የአዲስ አበባን የመሬት ዘረፋ የአዘዘው መለስ ዜናዊ ዛሬ ለአሻንጉሊት የተሠራች በምትመስል ቪላ ውስጥ በሥላሴ ቅጥር ግቢ ውስጥ ከሚገባው በላይ ድርሻውን ይዞአል፤ የሁሉም መጨረሻ ይኸው ነው፤ ኤርምያስ እንደሚነግረን የአዲስ አበባ የመሬት ዝርፊያ ከልማት ጋር የተያያዘ ሳይሆን ከዓመታት በፊት የነፍጠኞችን አከርካሪት ለመስበርና የወያኔን ትንሽ ልብ አፍኖ የያዘውን ጥላቻ ለማስተናገድ የታቀደ የሕመም መግለጫ ነው፤ ከኢትዮጵያ ሕዝብ አምስት ከመቶው ዓለም-አቀፍነት ሀበታምነት ደረጃ ላይ ሲደርስ ዘጠና አምስት ከመቶ የሚሆነው ደግሞ ወደለማኝነት ደረጃ ሲወርደ ምንም አይሆንም ብሎ ማሰብ — አይ ማሰብ የት አለ — መመኘት ሳያስቡት በድንገት የሚመጣውን የሕዝብንም፣የእግዚአብሔርንም ኃይል፤ አሜሪካ ተማሪ በነበርሁበት ዘመን (በድንጋይ ዳቦ ዘመን!) አንድ ተወዳጅ ዘፈን ነበር፡– ከቀኜ ብታመልጥ ከግራዬ አታመልጥም! የሚል።

ልማት ምንድን ነው? ከመጀመሪያውኑ መጠየቅ የነበረብን ጥያቄ ነው፤ እያንዳንዱ ሰው ኑሮውን ለማሻሻል፣ ከዛሬው ኑሮ ተምሮ ነገን የተሻለ ለማድረግ ብቻውን ወይም ከሌሎች ጋር በመተባበር የሚያደርገው ጥረት ነው፤ የኢትዮጵያ ሕዝብ መክሸፍ ጎልቶ የሚታይበት የቁሞ መቅረት ጉዳይ ነው፤ እውነቱ ግን ቁሞ መቅረት አይደለም በአንጻራዊ መለኪያ ቁልቁለት መውረደረ ነው፤ እዚህ ላይ ቆም ብለን የሩቁን መክሸፍ ከቅርቡ መክሸፍ ለይተን እንመልከተው።

ዱሮ ከአክሱም ሐውልቶችና ከላሊበላ ሕንጻዎች ብንጀምር የመክሸፍ ተዳፋቱ ከባድ ነው፤ ከአክሱምና ላሊበላ የሕንጻ ሥራዎች ወደጭቃ ጎጆ ያለው ቁልቁለት ነው፤ ወደቅርብ ዘመን መጥተን በእኔ ዕድሜ የሆነውን ብናይ ወደ1950 አካባቢ ኢትዮጵያ በማናቸውም ነገር የአፍሪካ መሪ ሆና ነበር፤ ዛሬ ያለችበትን ሁሉም ያውቀዋልና አልናገርም፤ ልማት የሚባለውን ነገር ገና አልጀመርንም፤ ልማት በዝርፊያ፣ ልማት በትእዛዝ አይመጣም፤ ልማት የምንለው የማኅበረሰቡን እድገት እንጂ የጥቂት ሰዎችን መንደላቀቅ አይደለም፤ ልማት የምንለው ከእያንዳንዱ ዜጋ ነጻነትና ፈቃድ ጋር የተያያዘውን የጋራ እድገት እንጂ በጥቂት ጉልበተኞች የአገሩን ዜጎች በአገራቸው ስደተኞች የሚያደርገውን አፍርሶ መሥራት አይደለም።

ግንቦት 2006

(ምንጭ: Mesfin Wolde-Mariam Blog)

Print Friendly, PDF & Email

60

SHARES
Share on Facebook
Tweet
Follow us
Share
Share
Share
Share
Share

Filed Under: Opinions Tagged With: Left Column

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • ጃዋርና በቀለ መታሠራቸው ተሰማ June 30, 2020 09:17 am
  • አገራዊ መድረክ ውጪ ድብቅ ውይይትን አንቀበልም June 17, 2020 06:57 am
  • ዴክሳሜታሶን! የኮሮና መድሀኒት June 17, 2020 06:49 am
  • የሰኔ 14ቱ ቀለበታዊ የፀሃይ ግርዶሽ በኢትዮጵያ! June 17, 2020 06:38 am
  • የግብፅ የአባይን ውሃ ብቻዬን ልጠቀም ግትር አቋም ድርድር እንቅፋት ሆኗል June 10, 2020 07:15 am
  • የቴድሮስ “ሥልጣን” – የመጨረሻው መጀመሪያ!? April 12, 2020 02:48 am
  • በብዛት የትግራይ ተወላጆች የሚጠቀሙበት የኤርትራ ስደተኛ ካምፕ ሊዘጋ ነው March 18, 2020 08:37 pm
  • እየተፈረካከሰ ያለው አንጋፋው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ March 18, 2020 08:09 pm
  • ኮሮና አዲስ ጉድ መዘዘ – ከቻይና በፊት በአሜሪካ ቁጥራቸው የማይታወቅ ሰዎችን ቀጥፏል March 16, 2020 11:41 pm
  • የኮንዶሚኒየም ቤቶች በደላሎችና በመመሪያ ሰጪዎች ኔትዎርክ እየተቸበቸበ ነው! ታከለ የት ናቸው? March 9, 2020 10:18 am
  • ኤርሚያስ ለገሠ ከባለአደራ ተባረረ March 9, 2020 08:09 am
  • ድፍድፍ ሲቀል ይንሳፈፋል፤ ምሁር ሲዘቅት ይመራል፥ March 7, 2020 11:24 pm
  • ኢትዮጵያዊ ምን ይመስላል? በምንስ ይመሰላል? March 7, 2020 10:29 pm
  • WHY I WROTE “MONEY, BLOOD AND CONSCIENCE” March 4, 2020 11:15 pm
  • አድዋ፤ የጥቁር ሕዝብ ድል! March 2, 2020 11:24 am
  • ፊታውራሪ ገበየሁ ገቦ (አባ ጎራው) March 2, 2020 11:12 am
  • የኦነግ ሁለት መልክና ሦስት ግብሮች – ቃርሚያው ኃይል ቅጥር ነፍሰገዳይ ሆኗል February 25, 2020 11:26 pm
  • በቡራዩ “የጃል ማሮ” ፎቶ ጨረታ አፈናከተ፤ “ቡራዩ ሆኖ ከሃዲን ማሞካሸት አይቻልም” ነዋሪዎች February 17, 2020 09:13 pm
  • “ዲቃላ” የፍረጃ ፖለቲካ በኦሮሚያ የኃይል አሰላለፉን እየቀየረ ነው February 13, 2020 11:58 pm
  • “ከዚህ በኋላ ማናቸውንም በወንጀል ድርጊት ውስጥ የሚሳተፉ አካላትን” አንታገስም – ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ February 13, 2020 05:07 pm
  • “እኛ ማንም ተሳዳቢ እንዲመጣብን አንፈልግም” የጅማ ነዋሪ February 13, 2020 09:28 am
  • “ወላጆቻችሁ ሰላማዊ ሰልፍ በሕዝቡ ያስደርጉልን” – አጋቾች February 11, 2020 07:53 pm
  • “ወንጀል የፈጸመም ያስፈጸመም ተይዞ ለህግ ይቀርባል፤ ምርመራም ተጀምሯል” February 11, 2020 06:59 pm
  • ጃዋር ወደ መጨረሻው “የትግል” ስልቱ – አማራን ማበጣበጥ! February 10, 2020 11:54 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2026 · Goolgule