• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

አቶ ኤርሚያስ አመልጋ በዚህ ወር መጨረሻ እንደሚመጡ ተጠቆመ

August 22, 2013 09:28 pm by Editor Leave a Comment

በአገር ውስጥና በውጭ አገር ለሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ቪላ ቤቶችንና አፓርትመንቶችን በተወሰነ ጊዜ ሠርተው ለማስረከብ ሩብ፣ ግማሽና ሙሉ ክፍያ ከተቀበሉ በኋላ፣ ምክንያቱ ግልጽ ባልሆነ ሁኔታ ከአገር የወጡት የአክሰስ ሪል ስቴት የቦርድ ሊቀመንበርና ዋና ሥራ አስኪያጅ የነበሩት አቶ ኤርሚያስ አመልጋ፣ በዚህ ወር መጨረሻ ላይ ወደ አገር ቤት እንደሚመለሱ ተጠቆመ፡፡

አቶ ኤርሚያስ ከአገር ከወጡ በኋላ ሳይመለሱ በዚያው የቀሩት፣ ቤት ሊገነቡላቸው የተዋዋሉዋቸው ሰዎች ቁጣና ዛቻን ብቻ ፈርተው ሳይሆን፣ አገር ቤት በነበሩበት ጊዜ ‹‹ግንባታው ይቅርብን ገንዘባችንን መልስ›› ላሏቸው ቁጥራቸው በውል ለማይታወቅ ሰዎች በጻፉት ደረቅ ቼክ ምክንያት መሆኑን ላነጋገሯቸው የቅርብ ጓደኞቻቸውና ወዳጆቻቸው መናገራቸው ተገልጿል፡፡ አቶ ኤርሚያስ ለደንበኞቻቸው የሰጧቸው ቼኮች ደረቅ በመሆናቸው በወንጀል እንደሚያስጠይቃቸው ስለሚያውቁ፣ በራሳቸውና በጓደኞቻቸው አማካይነት ቼክ የሰጧቸውን ደንበኞች በማነጋገር፣ የተቀበሉትን ገንዘብ ለመመለስ በመመስማማት ላይ መሆናቸውንና ክፍያውንም እንዳጠናቀቁ በዚህ ወር መጨረሻ እንደሚመለሱ መናገራቸውን፣ በቅርቡ የተቋቋመው ዓብይ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ አክሎግ ሥዩም ገልጸዋል፡፡

እንደ አቶ አክሎግ ገለጻ፣ አቶ ኤርሚያስ የሚያዋጣቸው ወደ አገር ቤት ተመልሰው ለሠሩት ጥፋት ይቅርታ በመጠየቅ፣ ለተፈጠረው ችግር ከተጎጂዎች ጋር በመሆን መፍትሔ ማፈላለግ ነው፡፡ ይኼንን ባያደርጉ ግን በኢንተርፖል በኩል ተይዘው ታስረው እንደሚመጡ እሙን ነው ይላሉ፡፡ ከሁለት ሺሕ በላይ የሚሆኑ ተጎጂዎች ለፌዴራል ፖሊስ ያስገቡት ደብዳቤ፣ በቅርቡ ለተሾሙት የፌዴራል ፖሊስ ጄነራል ዳይሬክተር አቶ አሰፋ በዩ ደርሷቸው እያዩትና በቅርቡም ተግባራዊ ሊያደርጉት እንደሚችሉ ተናግረዋል፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የዳያስፖራ ዴስክም (ከ130 በላይ ዳያስፖራዎች ተጎጂዎች ናቸው) ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥቶ እየተንቀሳቀሰ መሆኑንና መንግሥት ልዩ ትኩረት የሰጠው በመሆኑ፣ ለአቶ ኤርሚያስ የሚያዋጣቸው ራሳቸው ተመልሰው በመምጣት የችግሩን መፍቻ መንገድ አብረው ቢፈልጉ እንደሚሻል አቶ አክሎግ አክለዋል፡፡

ሌላው አቶ አክሎግ የገለጹት፣ የተጎጂዎቹን ገንዘብ የያዙና ከአክሰስ ጋር ይሠሩ የነበሩ ድርጅቶች ገንዘቡን ለመመለስና አብረውም ችግሩን በጋራ ለመፍታት የሚፈልጉ መኖራቸው ሲሆን፣ አንዳንዶቹ ደግሞ ‹‹አያገባንም›› ያሉ መኖራቸው ነው፡፡ ነገር ግን መንግሥት ሳይቀር የዜጎችን መጉላላትና መጎዳት ተመልክቶ እየተንቀሳቀሰ ባለበት ሁኔታ፣ የዜጎችን ገንዘብ ‹‹አያገባኝም›› በሚል ለማስቀረት መሞከራቸው ስለማያዋጣቸው፣ በሰላም ከተጎጂዎቹ ጋር በመሆን የወሰዱትን ገንዘብ በመመለስ የመፍትሔው አካል እንዲሆኑ የኮሚቴው ሰብሳቢ አቶ አክሎግ ጠይቀዋል፡፡

በሌላ በኩል ደግሞ ለአክሰስ ሪል ስቴት 40 ከመቶ ድርሻውን የሰጠውና 60 በመቶ የሚሆነው ከፍተኛ ባለድርሻ የሆነው ፓስፊክ ሊንክ ኢትዮጵያ ሪል ስቴት ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ‹‹ከአክሰስ ሪል ስቴት ጋር በመሆን ቪላና አፓርትመንት እገነባላችኋለሁ በማለት ውል ካስገባን በኋላ ውላችን ሳይፈጸምልን ገንዘባችንን ከወሰደ አንድ ዓመት ሞልቶታል፤›› በሚል፣ 137 ደንበኞች የ73,388,844 ብር ከ50 ሳንቲም ክስ መሥርተውበታል፡፡ ክሱ የተመሠረተው በፓስፊክ ሊንክ ኢትዮጵያ ሪል ስቴት፣ በአክሰስ ሪል ስቴት በአቶ ነብዩ ሳሙኤልና በአቶ ኤርሚያስ አመልጋ ላይ ነው፡፡

የክሱ ዋና መነሻ ፓስፊክ ሊንክ ኢትዮጵያ ሪል እስቴት በየካ ክፍለ ከተማ የቀድሞ ቀበሌ 20/21 አያት ኢስት ቪው (መሪ) አካባቢ በወሰደው 50 ሺሕ ካሬ ሜትር የሊዝ ቦታ ላይ ይገነባል የተባለው ቪላና አፓርትመንት ነው፡፡ ጉዳት እንደደረሰባቸው በመግለጽ ክስ የመሠረቱት 137 ደንበኞች ከፓስፊክ ሊንክና አክሰስ ጋር በፈጸሙት ውል መሠረት፣ በ14 ወራት ውስጥ ቤቱን ገንብተው ሊያስረክቧቸው ውል የገቡ ቢሆንም፣ እንኳን ቤት ሊገነቡ ቀርቶ ግንባታ ካቆሙ አንድ ዓመት እንደሞላቸው በክሱ ጠቅሰዋል፡፡ የተወሰኑ የተጀመሩ ቤቶችን አጠናቀው ለተወሰኑት ከማስረከብ ባለፈ ሌላውን እንደማይችሉ እንደገለጹላቸውም ከሳሾቹ አክለዋል፡፡ ሪል ስቴቶቹ በአንድነትና በነጠላም ኃላፊነት እንዳለባቸውና አቶ ነብዩ ሳሙኤልና አቶ ኤርሚያስ አመልጋ የድርጅቶቹ ሥራ አስኪያጅ በመሆናቸው ተጠያቂ እንደሚሆኑም በክሱ ተካቷል፡፡

የአክሰስ ሪል ስቴት ዋና ሥራ አስኪያጅ የነበሩት አቶ ኤርሚያስ ለፍርድ ቤቱ ምላሽ ባይሰጡም፣ የፓስፊክክ ሊንክ ኢትዮጵያ ሪል ስቴት ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ነብዩ ሳሙኤል ፍርድ ቤት ቀርበው ምላሽ መስጠታቸውን ገልጸዋል፡፡ የታዋቂው ጋዜጠኛ ሳሙኤል ፈረንጅ የመጀመሪያ ልጅና የኢትዮጵያ ብስክሌት ፌዴሬሽን የበላይ ጠባቂ የሆኑት አቶ ነብዩ፣ በአሜሪካ ለ23 ዓመታት ከቆዩ በኋላ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ ዳያስፖራዎች ወደ አገራቸው ገብተው ኢንቨስት ማድረግ እንዳለባቸው ያደረጉትን ጥሪ ተከትሎ፣ እ.ኤ.አ ኦገስት 11 ቀን 2003 ወደ ትውልድ አገራቸው መመለሳቸውን ገልጸዋል፡፡

እሳቸው ወደ አገር ቤት በተመለሱበት ወቅት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ዳያስፖራዎችን ያበረታታ የነበረው በሪል ስቴት የሥራ መስክ እንዲሰማሩ ስለነበር፣ እሳቸውም ‹‹ፓስፊክ ሊንክ ኢትዮጵያ ሪል ስቴት›› የሚል ድርጅት አቋቁመው አያት መሪ አካባቢ 50 ሺሕ ካሬ ሜትር ቦታ መውሰዳቸውን ገልጸዋል፡፡ ከሌሎች ከሚሠሯቸው ቢዝነሶች ጎን ለጎን የቤት ልማት ፕሮግራሙን ለማካሄድ ከአስተዳደሩ በፊት በዋነኛነት ያነሳሳቸው፣ የቢዝነስና ኮንስትራክሽን ባንክ በወቅቱ 30 በመቶ መክፈል ለሚችል ሪል ስቴት አልሚ 70 በመቶ ብድር እንደሚሰጥ በማስታወቁ መሆኑን አቶ ነብዩ አውስተዋል፡፡

ፓስፊክ ሊንክ 50 ሺሕ ካሬ ሜትሩን በካሬ ሜትር 401 ዶላር ሒሳብ 250 ሺሕ ዶላር ከፍለው ለ20 ዓመታት የሊዝ ውል መፈጸሙን  የገለጹት አቶ ነብዩ፣ የወሰዱትን ቦታ አስተካክለው ወደ ግንባታ እንደገቡ 70 በመቶ ብድር እንደሚሰጥ ቃል ገብቶ የነበረው ኮንስትራክሽንና ቢዝነስ ባንክ፣ እሰጣለሁ ያለውን ብድር መተውን በመግለጹ የፋይናንስ ችግር አጋጥሞት እንደነበር አስረድተዋል፡፡ በወቅቱ (ከሦስት ዓመት በፊት) ሊቪንግ ስቲል (አሁን ይበል ኮንስትራክሽን ተብሏል) ለሚባል ድርጅት ሙሉ ፋይናንስ የሚያቀርብለት አክሰስ ሪል ስቴት መሆኑን በጓደኞቻቸው አማካይነት ያወቁት አቶ ነብዩ፣ እሳቸውም የሪል ስቴቱን ባለቤት አቶ ኤርሚያስን አግኝተው ቢያነጋግሯቸው ሊረዷቸው እንደሚችሉ ሲነገራቸው አቶ ኤርሚያስን ሊተዋወቋቸው መቻላቸውን ተናግረዋል፡፡ ሊቪንግ ስቲል የሚባለው ድርጅትን አክሰስ ሙሉ በሙሉ ፋይናንስ አድርጎት ይሠራ ስለነበር፣ አቶ ነብዩ አቶ ኤርሚያስን ሲያነጋግሯቸው ፈቃደኛ በመሆናቸው፣ ሥራውን ለመሥራት በሕጋዊ መንገድ በውልና ማስረጃ መዋዋላቸውን አክለዋል፡፡

ፓስፊክ ሊንክና አክሰስ ያደረጉት ውል የሕንፃ ግንባታ ወጪው ስለማይታወቅ ግንባታውን ሲጨርሱ ወጪያቸውን በማስላት ትርፉን አክሰስ 40 ከመቶ እንዲወስድና ፓስፊክ ሊንክ 60 ከመቶ ሊወስድ በመስማማት ሥራ መጀመራቸውን አቶ ነብዩ ገልጸዋል፡፡ ፓስፊክ ሊንክ የባንክ ሒሳቡ ኅብረት ባንክ ቢሆንም ለሪል ስቴት ሥራው አመቺ እንዲሆን የሚል ጥያቄ አቶ ኤርሚያስ በማቅረባቸው ዘመን ባንክ ሒሳብ እንዲከፍትና በአቶ ኤርሚያስ ብቻ እንዲንቀሳቀስ ማድረጋቸውን የገለጹት አቶ ነብዩ፣ ፓስፊክ ሊንክ ከስምምነታቸው ውጭ ቤት እንዳይሸጡ ደረሰኞቻቸው በማይከፈት ካዝና ውስጥ እንዲቀመጥ ማድረጋቸውንና ለአንዳንድ ሥራ አመቺ እንዲሆን በማለት የፓስፊክ ማህተምንም በዕምነትና በፊርማ ለአቶ ኤርሚያስ መሰጠቱን ገልጸዋል፡፡

ሁሉንም ውል ወይም ስምምነት ሲያደርጉ ብቻቸውን ሳይሆን አሁን ከሳሽ ለሆኑት ቤት ገዢዎች ጠበቃ የሆኑ ግለሰብን እያማከሩና እሳቸው ያሏቸውን (ቀድሞ የእሳቸው ተቀጣሪ ጠበቃ ነበሩ) ማድረጋቸውን የገለጹት አቶ ነብዩ፣ በመሀል ላይ መንግሥት የሪል ስቴት ሥራን ለጊዜው ሲያስቆም ከመቆሙ በስተቀር ያለምንም ችግር ይሠሩ እንደነበር ተናግረዋል፡፡ አክሰስ ሪል ስቴት አሁን በፈጠረው ችግር ውስጥ ፓስፊክ ሊንክ ምንም የሚያውቀውና የተሳተፈበት ነገር እንደሌለ የገለጹት አቶ ነብዩ፣ አክሰስ ግንባታ ሲያቆም ‹‹ለምን?›› የሚል ጥያቄ ሲያነሱ ‹‹ግንባታው የጥራት ጉድለት ስላለበት፣ ጥራትን በሚመለከት የእኛና የመንግሥት መሀንዲሶች ቻይና ተልከው እያጠኑት ስለሆነ፣ እነሱ እስከሚመለሱ እንዲቆም ተደርጓል፤›› ሲሏቸው ዝም ብለው ማለፋቸውን አስረድተዋል፡፡

አቶ ነብዩ አብዛኛውን ጊዜያቸውን የሚያሳልፉት አሜሪካ መሆኑን ተጠቅመው አቶ ኤርሚያስ በእምነት የሰጧቸውን ደረሰኞችና ማህተም በመጠቀም ቤት ይሸጡ እንደነበር የተረዱትም ፍርድ ቤት ተከሰው ማስረጃ ሲቀርብባቸው መሆኑን ተናግረዋል፡፡ መከሰሳቸውን ሰምተው ሲመጡ የሰሙትንና የተደረገውን ማመን ቢያቅታቸውም፣ ፍርድ ቤት ቀርበው የቀረበባቸውን ክስ ከሰሙ በኋላ ለክሳቸው ምላሽ መስጠታቸውን አስረድተዋል፡፡

ክስ ከመሠረቱባቸው የአክሰስ ደንበኞች ውስጥ አምስት በመቶ የሚሆኑት ብቻ መሆናቸውን የገለጹት አቶ ነብዩ፣ ከ95 በመቶዎቹ ጋር ቀርበው በመነጋገር ፓስፊክ ከያዘው ቦታና ሌሎች የአክሰስ ቦታዎችን አንድ ላይ በማልማት ችግሩን በጋራ ለመፍታት እየሠሩ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ አዲስ የተቋቋመው ኮሚቴና አዲሱ የአክሰስ ሪል ስቴት ቦርድም መስማማታቸውንና ችግሩን ለመፍታት አብረው ከመሥራት በዘለለ አቶ ኤርሚያስ ወደ አገር ቤት ተመልሰው ችግሩን አብረዋቸው እንዲፈቱ ጥረት እያደረጉ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡

‹‹በአገሬ ላይ የቻልኩትን ያህል አስተዋጽኦ አደርጋለሁ ብዬ ከ23 ዓመታት የውጭ አገር ቆይታ በኋላ ስመለስ ስሜን በማይሆን ነገር እንዲጠፋ አልፈልግም፤›› ያሉት አቶ ነብዩ፣ ወደ ፍርድ ቤት የሄዱት ደንበኞች ክሳቸውን አቋርጠው በጋራ ሆነው ችግሩን የሚፈቱበትን መንገድ ቢፈልጉ ደስታቸው ቢሆንም፣ ‹‹ሕግን ተከትለን መሆን ያለብንን እንሆናለን›› የሚሉ ከሆነ ግን መብታቸው መሆኑን ተናግረዋል፡፡ እነሱ ከአክሰስ ጋር ያደረጉትን ውል ፓስፊክ ሊንክ ኢትዮጵያ ዕውቅና ሊሰጥ እንደማይችል የገለጹት አቶ ነብዩ፣ ተስማምቶ በመሥራት ቸግርን ማቃለል ተገቢ መሆኑን አምኖበት ከሚመጣ ጋር ለመሥራት ግን ፈቃደኛ መሆናቸውን አስታውቀዋል፡፡ (ምንጭ: ሪፖርተር)

Print Friendly, PDF & Email

60

SHARES
Share on Facebook
Tweet
Follow us
Share
Share
Share
Share
Share

Filed Under: Social Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • ጃዋርና በቀለ መታሠራቸው ተሰማ June 30, 2020 09:17 am
  • አገራዊ መድረክ ውጪ ድብቅ ውይይትን አንቀበልም June 17, 2020 06:57 am
  • ዴክሳሜታሶን! የኮሮና መድሀኒት June 17, 2020 06:49 am
  • የሰኔ 14ቱ ቀለበታዊ የፀሃይ ግርዶሽ በኢትዮጵያ! June 17, 2020 06:38 am
  • የግብፅ የአባይን ውሃ ብቻዬን ልጠቀም ግትር አቋም ድርድር እንቅፋት ሆኗል June 10, 2020 07:15 am
  • የቴድሮስ “ሥልጣን” – የመጨረሻው መጀመሪያ!? April 12, 2020 02:48 am
  • በብዛት የትግራይ ተወላጆች የሚጠቀሙበት የኤርትራ ስደተኛ ካምፕ ሊዘጋ ነው March 18, 2020 08:37 pm
  • እየተፈረካከሰ ያለው አንጋፋው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ March 18, 2020 08:09 pm
  • ኮሮና አዲስ ጉድ መዘዘ – ከቻይና በፊት በአሜሪካ ቁጥራቸው የማይታወቅ ሰዎችን ቀጥፏል March 16, 2020 11:41 pm
  • የኮንዶሚኒየም ቤቶች በደላሎችና በመመሪያ ሰጪዎች ኔትዎርክ እየተቸበቸበ ነው! ታከለ የት ናቸው? March 9, 2020 10:18 am
  • ኤርሚያስ ለገሠ ከባለአደራ ተባረረ March 9, 2020 08:09 am
  • ድፍድፍ ሲቀል ይንሳፈፋል፤ ምሁር ሲዘቅት ይመራል፥ March 7, 2020 11:24 pm
  • ኢትዮጵያዊ ምን ይመስላል? በምንስ ይመሰላል? March 7, 2020 10:29 pm
  • WHY I WROTE “MONEY, BLOOD AND CONSCIENCE” March 4, 2020 11:15 pm
  • አድዋ፤ የጥቁር ሕዝብ ድል! March 2, 2020 11:24 am
  • ፊታውራሪ ገበየሁ ገቦ (አባ ጎራው) March 2, 2020 11:12 am
  • የኦነግ ሁለት መልክና ሦስት ግብሮች – ቃርሚያው ኃይል ቅጥር ነፍሰገዳይ ሆኗል February 25, 2020 11:26 pm
  • በቡራዩ “የጃል ማሮ” ፎቶ ጨረታ አፈናከተ፤ “ቡራዩ ሆኖ ከሃዲን ማሞካሸት አይቻልም” ነዋሪዎች February 17, 2020 09:13 pm
  • “ዲቃላ” የፍረጃ ፖለቲካ በኦሮሚያ የኃይል አሰላለፉን እየቀየረ ነው February 13, 2020 11:58 pm
  • “ከዚህ በኋላ ማናቸውንም በወንጀል ድርጊት ውስጥ የሚሳተፉ አካላትን” አንታገስም – ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ February 13, 2020 05:07 pm
  • “እኛ ማንም ተሳዳቢ እንዲመጣብን አንፈልግም” የጅማ ነዋሪ February 13, 2020 09:28 am
  • “ወላጆቻችሁ ሰላማዊ ሰልፍ በሕዝቡ ያስደርጉልን” – አጋቾች February 11, 2020 07:53 pm
  • “ወንጀል የፈጸመም ያስፈጸመም ተይዞ ለህግ ይቀርባል፤ ምርመራም ተጀምሯል” February 11, 2020 06:59 pm
  • ጃዋር ወደ መጨረሻው “የትግል” ስልቱ – አማራን ማበጣበጥ! February 10, 2020 11:54 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2026 · Goolgule