• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

የቂሊንጦ እስር ቤት ቃጠሎ ለህወሃት ፈተና ተጨማሪ ነዳጅ ሆነ!!

September 4, 2016 11:05 am by Editor 1 Comment

የኢትዮጵያ ፖለቲካ ቀውስ ከቀን ወደቀን እየጋመ ነው። ህወሃት ችግሮችን በሰከነ መንፈስ ከመፍታት ይልቅ ክተት አውጆና ንጹሃንን እየፈጀ ይገኛል። ሥልጣን ከያዙ ጀምሮ የረባ ትዕዛዝ ሰጥተው የማያውቁት ሃይለማርያም “አዝዣለሁ” ሲሉ በወገኖቻቸው ላይ ሞት አውጀው ቀውሱን አግመውታል። አፍቃሪ ህወሃቶችም የ“ቅምጡን ባሪያ ጠቅላይ ሚኒስትር” “ትዕዛዝ” ተከትለው “ትዕግስትም ገደብ አለው” እያሉ በየሚዲያውና በማህበራዊ ገጾች እያሽካኩ ነው። ሕዝብ “መሳሪያ አጣን” እያለ ጥሪ እያቀረበ ነው። ያም ሆኖ ምሬት የገፋቸው ሁሉ አመጹን ገፍተውበታል።

በከፋፍለህ ግዛ የፖለቲካ ቁማር ህዝብ እያናከሰ ላለፉት 25 ዓመታት አገር ሲገዛ የኖረው ህወሃት ዛሬ አደረጃጀቱና “አጋሬ” የሚላቸው የተለዩት ይመስላሉ። ኦህዴድ ከተናጋና ከከዳ ሰንብቷል። ብአዴንም መመኪያ ሊሆን የማይችልበት ደረጃ ደርሷል። ለዚህም ይመስላል በይፋ ባይታወጅም ሁለቱ ክልሎች በወታደራዊ አስተዳደር ሥር ወድቀዋል።

በተለይ የአማራ ክልል ሙሉ በሙሉ በወታደራዊ አገዛዝ ስር መወደቁ ይፋ ከሆነበት ቀን ጀምሮ በስም የሚታወቁ ከ70 በላይ ሰዎች በትግራይ ሕዝብ ነጻአውጪ ግምባር (ህወሃት) ገዳይና አልሞ ተኳሾች የከበረው ህይወታቸው ተቀጥፏል። ህጻናት፣ አዛውንት፣ ወጣቶች፣ ሴቶች በግፍ ተገድለዋል፤ በጅምላ ታስረዋል። እስር ቤት አልበቃ ብሎ ትምህርት ቤቶች ማጎሪያ ሆነዋል። በየአቅጣጫው የሚወጡ መረጃዎች እንደሚያረጋግጡት የታፈኑ፣ ተረሽነው በጅምላ የተቀበሩ፣ የተሰወሩ፣ ቤተሰብ እርም ያላወጣላቸው በርካታ ናቸው። ከሁሉም በላይ በሽሽት ዱር የገቡ ቁጥር ስፍር እንደሌላቸው ለቪኦኤና ለኢሳት መረጃ ከሚሰጡ ለማረጋገጥ ተችሏል። የዝግጅት ክፍላችንም በርካታ መረጃዎች ደርሰውታል።

በኦጋዴን ዙሪያው ተዘግቶ እንደተካሄደው ጭፍጨፋ፣ ዛሬም ዓለም መረጃ እንዳይደርሰው ኢንተርኔትና ስልክ ተጠርቅሞ አማራ ክልል በጅምላ የሚካሄደው ጭፍጨፋ ምን ያህል የከፋ እንደሆነ ወደ ስፍራው ሲጓጓዙ ከነበሩት መሳሪያዎች አይነትና ክብደት ለመረዳት እንደሚቻል ብዙዎች እያነቡ ነው የሚገልጹት። ባዶ እጃቸውን ተቃውሞ የሚያሰሙ ወገኖችን ለጥያቄያቸው ህጋዊ መልስ ከመስጠት ይልቅ “ህልሜ እስኪፈጸም እኔ ካልገዛኋችሁ እትብታችሁ በተቀበረበት ቦታም ቢሆን የመኖር ተስፋ የላችሁም” በሚል ጸጉረ ልውጥ ቅጥር ነፍሰ ገዳዮች ተመድበውላቸው በጅምላ እየተፈጁ መሆኑንን ሰለባዎች በሃዘን እየገለጹ ነው። ባገራቸው ምድር እየተለቀሙ በውል በማይታወቅ ማጎሪያ እየታጎሩ ነው።

“ተራራ ያንቀጠቀጠ” እየተባለ ያለገድሉ ታሪክ ሲጻፍለት፣ ከበሮ ሲደለቅለት የኖረው ህወሃት አስቀድሞ በጋዜጠኛ ሲንቀጠቀጥ ኖሮ አሁን ደግሞ በሰላማዊ ሰልፈኛ ከተንቀጠቀጠ ወዲህ በረሃ የተከተበው የቀድሞው አውሬ ባህርዩ በይፋ እየታየ መጥቷል፡፡ የረሃብተኛ እህልን በጠራራ ጸሃይ በመዝረፍ የራሱን ወገን በጥይትና በረሃብ የቆላው ህወሃት፣ “ነጻ አወጣሃለሁ” የሚለውን ህዝብ በተለያዩ ስልታዊ መንገዶች በመጨፍጨፍ ሥልጣን የጨበጠው “የባለ ራዕዩ” ህወሃት፣ ከተማ መሃል ታክሲ ውስጥ ቦምብ በመጥመድ የንጹሃን ደም ያፈሰሰው አሸባሪው ህወሃት፣ … አልገዛም ያለውን ሕዝብ እየጨፈጨፈና እያፈነ ባለበት በአሁኑ ሰዓት አዲስና አስደንጋጭ ዜና መስማት ተጀምሯል። እስር ቤቶች እየጋዩ መሆናቸው!!

ቀደም ሲል አምቦ እስር ቤት ጋየ። የጉዳቱ መጠን በቅጡ ሳይታወቅ ተድበስብሶ ታለፈ። ከዚያም ጎንደር አንገረብ እስር ቤት ነደደ ተባለ። እዚያም የደረሰው ጉዳትና የጉዳቱ መጠን በቅጡ ሳይነግር ተሸፋፍኗል፤ አሁን ደግሞ ቂሊንጦ እስር ቤት ጋይቷል። ቃጠሎው እነ በቀለ ገርባን ጨምሮ  ታዋቂ የፖለቲካ አመራሮች፣ የሃይማኖት መሪዎች፣ የመብት ተከራካሪዎችና የስርዓቱ ሰለባዎች ስለሚገኙ ዜናው ህወሃት ለገጠመው ቀውስ እንደ ነዳጅ ሆነ። ቃጠሎው ይፋ መሆኑን ተከትሎ ቅድሚያ አቶ ጃዋር መሐመድ ይህንን አስደንጋጭ ማሳሰቢያ በፌስቡክ ገጹ ይፋ አደረገ።

ወያኔ በቀለ ገርባ እና ሌሎቹ አመራሮች በህይወት መኖራቸውን በሚቀጥሉት 3 ሰዓታት ውስጥ ተጨባጭ ማረጋገጫ ካልሰጠ የሚቀጥሉት እርምጃዎች ይወሰዳሉ

1) በሁሉም ደረጃ ያሉ እስር ቤቶች ይወድማሉ

2) ማንኛውም የወያኔ ንብረት ይወድማል

3) መንግዶች በሁሉም አቅጣጫ እና ሰፈር ይዘጋሉ (ኢንተርኔት ሊዘጉ ስለሚችሉ ይህን መልክት በአስቸኳይ አስተላልፉ) #oromoProtests

የኢህአዴግ አንደበት የሆነው ፋና ብሮድካስቲንግ አንድ ሰው መሞቱንና ስድስት መቁሰላቸውን የፌደራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት ጠቅሶ ዘገበ። በቴሌቪዥን ስርጭትም ተመሳሳይ ዜና ቀርቦ ዝርዝሩ ሲጣራ እንደሚቀርብ ተጠቆመ። ዜናው ሽባ በመሆኑና ጥርት ያለ መረጃ የሚሰጥ ሆኖ ባለመገኘቱ አሁንም ጃዋር እንዲህ ሲል በድጋሚ በፌስቡክ ገጹ ማስጠንቀቂያ ሰጠ።

“በቂሊንጦ እስርቤት የተኩስና እሳት አደጋ መኖሩ ለህዝብ ጆሮ ከደረሰ 12 ሰአታት አለፉት። መንግስት ቢያንስ የፖሊቲካ መሪዎቹን ደህንነት እንዲሳውቅ ከተጠየቀ ሶስት ሰዓታት አለፉ። እስካሁን መሪዎቹ ደህና ስለመሆናቸው ለቤተሰቦቻቸው፤ ለጠበቆቻቸውም ሆነ ለህዝብ ምንም አልተነገረም። ይህ ዝምታ በአመራሩ ላይ የከፋ አደጋ ለመድረሱ አመላካች ነው። አዲስ ፎርቹን ቢያንስ 20 ሰዎች መገደላቸውን ዘግቧል። መሪዎቻችን ከነዚህ የአረመኒያዊ ጭፍጨፋው ሰለባ ላለመሆናቸው ምንም ማረጋገጫ የለም። እናም ህዝባችን በቻለው መንገድ ሁሉ እርምጃ መውሰድ መብቱም ግዴታውም ነው!”

“ንገሩን!! የት እንዳሉና በምን ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ ንገሩን። ወይም ሞተው ከሆነ አስከሬናቸውን ስጡን” ሲሉ የአቶ በቀለ ገርባ ባለቤት ወ/ሮ ሃና በስልክ እንደነገሩት የገለጸው ኤሊያስ ገብሩ ጎዳና ወ/ሮ ሃና ስለባለቤታቸው የተናገሩትን ጨምሮ ዘግቦ ነበር፡፡ “ከበቀለ ጋር ባሳለፍነው ሐሙስ ቂሊንጦ ተገናኝተን በሰላም ተነጋገረን ነበር። ትናንት ለጥየቃ መግባት አልቻልኩም። ዛሬ ልጃችን ቦንቱ ሄዳ ነበር። ረፋድ ላይ በቂሊንጦ በተነሳው ቃጠሎና ተኩስ ምክንያት ደውላለኝ ተነጋግረናል። ቀኑን ሙሉ በአካባቢው ብትገኝም አባቷን መጠየቅ ሳትችል ወደቤት ተመልሳለች። በቀለም ሆነ ሌሎች በቂሊንጦ እስር ቤት ያሉ ወገኖቻችን በምን ሁኔታ ላይ እንዳሉ ማወቅ አልቻልንም። ነገ እኔና ልጄ ቂሊንጦ እንሄዳለን …” ሲሉ ከቃጠሎው በኋላ ስሜታቸውን ገልጸዋል።

በተለያዩ ወገኖች የሚወጡ መረጃዎች እንደሚያስረዱት የቂሊንጦ ማጎሪያ ቃጠሎ ከመታየቱ በፊት ተኩስ ይሰማ ነበር። በእስረኞች በኩል እስርቤቱን ደርምሶ ለመወጣት ሙከራ መደረጉን ህወሃት ደጋፊዎች ይናግራሉ፡፡ ከቃጠሎው በኋላ 22 የሚጠጉ ሰዎች መሞታቸውና በውል የማይታወቁ ክፉኛ ተጎድተው ጦር ሃይሎች ሆስፒታል መግባታቸው ተሰምቷል። ህይወታቸው አለፈ የተባሉትን 22 ሰዎች ጳውሎስ ሆስፒታል እንደተረከበ የሚገልጹ ወገኖች “አስከሬኖቹ በመከላከያ ወታደሮች ታጅበው ነበር” ብለዋል። እሁድ ማለዳው ላይ በማኅበራዊ ድረገጾች የተሰራጨ መረጃ የሟቾች ቁጥር 50 መድረሱ ሲገልጽdaniel berhane በይፋ ባይረጋገጥም አቶ በቀለ ገርባ በህይወት መኖራቸው ተነግሯል፡፡ የሟቾች ማንነት እስከአሁን ለማወቅ አልተቻለም፡፡

አሳዛኙ የእስርቤት ቃጠሎ በተሰማ ጊዜ ዳንኤል ብርሃኔ የሚባል የህወሃት ደጋፊ ያለ እረፍት በፌስቡክ ገጹ በሚለቀው መረጃ ላይ በቃጠሎው ሚኒስትር ዴኤታዎች እንዳሉበት ገልጾ ነበር፡፡ “ስም ዝርዝ(ራቸውን) እንደአስፈላጊነቱ በይፋ እንለቃለን” በማለት በራሱ ገጽ ላይ እንደብዙ ሰው ተናገሯል፡፡ የህዝብ አልገዛም ባይነት ያስጨነቀው ህወሃት ባንድ ወር ሁሉን እናስተካክላለን በሚል “ተላላኪ፣ የውስጥ አርበኛ፣ አንጃ፣ …” በማለት ምሳ ሊያደርጋቸው ያሰበውን ተረኞች ዳንኤል ጌቶቹን ሳያስፈቅድ የፌስቡክ ቁርስ አድርጓቸዋል፡፡ መረጃውን እንደለቀቀ አንድ አገር ውስጥ የሚገኝ ታማኝ የመስመር ጋዜጠኛ “አፈርኩብህ” ሲል ጉዳዩ በምርመራ ሳይረጋገጥ የሚኒስትር ዴኤታዎችን ስም ከቃጠሎው ጋር ወንጅሎ ማቅረቡ አግባብ እንዳልሆነ አስተያየት ከሰነዘረበት በኋላ ቀለብ ሰፋሪ ጌቶቹ በሰጡት ቀጭን ትዕዛዝ መረጃውን ከፌስቡክ ገጹ ላይ አንስቶታል፡፡ “በጋዜጠኛነት” ታፔላ ፌስቡክ ላይ የሚክለፈለፍ አንድ ተራ ግለሰብ በአገር አስተዳደር ላይ የተሰየሙ ከፍተኛ ባለሥልጣናትን መፈጸማቸው ባልተረጋገጠ ወንጀል ስማቸውን ማጥፋቱ አግባብነት የለውም የሚሉ አስተያየት ሰጪዎች በሚኒስትር ደኤታነት የተቀመጡት ባለሥልጣናት ማስረጃውን በመያዝ ጉዳዩን ወደ ሕግ መውሰድ ይገባቸዋል በማለት ይመክራሉ፡፡


ማሳሰቢያ፤ በተለይ በስም ወይም በድርጅት ስም እስካልተጠቀሰ ድረስ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® ላይ የሚወጡት ጽሁፎች በሙሉ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ®ንብረት ናቸው፡፡ ይህንን ጽሁፍ ለመጠቀም የሚፈልጉ ሁሉ የዚህን ጽሁፍ አስፈንጣሪ (link) ወይም የድረገጻችንን አድራሻ (http://staging.goolgule.com/) አብረው መለጠፍ ከጋዜጠኛነት የሚጠበቅና ህጋዊ አሠራር መሆኑን ልናሳስብ እንወዳለን፡፡

Print Friendly, PDF & Email

60

SHARES
Share on Facebook
Tweet
Follow us
Share
Share
Share
Share
Share

Filed Under: News Tagged With: Full Width Top, Middle Column

Reader Interactions

Comments

  1. አለም says

    September 6, 2016 05:32 pm at 5:32 pm

    ዳንኤል ብርሃኔን እንደ ቁምነገረኛ መድረክ ሰጣችሁት? እስክንድር ነጋን ናዚ ነው ያለ አይደለም? ጎልጉልን ብሆን ጽሑፉን አልለጥፍለትም፤ እኩይ ሥራውን መሥራት ይሆናላ!

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • ጃዋርና በቀለ መታሠራቸው ተሰማ June 30, 2020 09:17 am
  • አገራዊ መድረክ ውጪ ድብቅ ውይይትን አንቀበልም June 17, 2020 06:57 am
  • ዴክሳሜታሶን! የኮሮና መድሀኒት June 17, 2020 06:49 am
  • የሰኔ 14ቱ ቀለበታዊ የፀሃይ ግርዶሽ በኢትዮጵያ! June 17, 2020 06:38 am
  • የግብፅ የአባይን ውሃ ብቻዬን ልጠቀም ግትር አቋም ድርድር እንቅፋት ሆኗል June 10, 2020 07:15 am
  • የቴድሮስ “ሥልጣን” – የመጨረሻው መጀመሪያ!? April 12, 2020 02:48 am
  • በብዛት የትግራይ ተወላጆች የሚጠቀሙበት የኤርትራ ስደተኛ ካምፕ ሊዘጋ ነው March 18, 2020 08:37 pm
  • እየተፈረካከሰ ያለው አንጋፋው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ March 18, 2020 08:09 pm
  • ኮሮና አዲስ ጉድ መዘዘ – ከቻይና በፊት በአሜሪካ ቁጥራቸው የማይታወቅ ሰዎችን ቀጥፏል March 16, 2020 11:41 pm
  • የኮንዶሚኒየም ቤቶች በደላሎችና በመመሪያ ሰጪዎች ኔትዎርክ እየተቸበቸበ ነው! ታከለ የት ናቸው? March 9, 2020 10:18 am
  • ኤርሚያስ ለገሠ ከባለአደራ ተባረረ March 9, 2020 08:09 am
  • ድፍድፍ ሲቀል ይንሳፈፋል፤ ምሁር ሲዘቅት ይመራል፥ March 7, 2020 11:24 pm
  • ኢትዮጵያዊ ምን ይመስላል? በምንስ ይመሰላል? March 7, 2020 10:29 pm
  • WHY I WROTE “MONEY, BLOOD AND CONSCIENCE” March 4, 2020 11:15 pm
  • አድዋ፤ የጥቁር ሕዝብ ድል! March 2, 2020 11:24 am
  • ፊታውራሪ ገበየሁ ገቦ (አባ ጎራው) March 2, 2020 11:12 am
  • የኦነግ ሁለት መልክና ሦስት ግብሮች – ቃርሚያው ኃይል ቅጥር ነፍሰገዳይ ሆኗል February 25, 2020 11:26 pm
  • በቡራዩ “የጃል ማሮ” ፎቶ ጨረታ አፈናከተ፤ “ቡራዩ ሆኖ ከሃዲን ማሞካሸት አይቻልም” ነዋሪዎች February 17, 2020 09:13 pm
  • “ዲቃላ” የፍረጃ ፖለቲካ በኦሮሚያ የኃይል አሰላለፉን እየቀየረ ነው February 13, 2020 11:58 pm
  • “ከዚህ በኋላ ማናቸውንም በወንጀል ድርጊት ውስጥ የሚሳተፉ አካላትን” አንታገስም – ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ February 13, 2020 05:07 pm
  • “እኛ ማንም ተሳዳቢ እንዲመጣብን አንፈልግም” የጅማ ነዋሪ February 13, 2020 09:28 am
  • “ወላጆቻችሁ ሰላማዊ ሰልፍ በሕዝቡ ያስደርጉልን” – አጋቾች February 11, 2020 07:53 pm
  • “ወንጀል የፈጸመም ያስፈጸመም ተይዞ ለህግ ይቀርባል፤ ምርመራም ተጀምሯል” February 11, 2020 06:59 pm
  • ጃዋር ወደ መጨረሻው “የትግል” ስልቱ – አማራን ማበጣበጥ! February 10, 2020 11:54 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2026 · Goolgule